መጋቢት 5 ፃድቁ አቡነ ገ/መንፈስ ቅዱስ ዓመታዊ ክብረ
በዓል በደመቀ ሁኔታ ተከብሮ ይውላል ።
በዚህ እለት እምናከብረው የእረፍት መታሰቢያቸውን ሲሆን
ከገድላቸውም እንዲህ ተፅፎ እናገኘዋለን ።
ፃድቁ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ የተወለዱት ግብፅ ንሂሳ
በምትባል ቦታ ከአባታቸው ስምዖን ከእናታው አቅሌስያ ነው።
በአጠቃላይ የኖሩበት ዕድሜ 562 አመት ሲሆን 300
ዓመቱን በግብጽ 262 ቱን በኢትዮጵያ 100 ዓመት በዝቋላ
በተጋድሎ ያሳለፉ ታላቅ አባት ናቸው።
መጋቢት 5 በገድለ አቡነ ገ/መንፈስ ቅዱስ
ዕለቱ ቅዳሜ ለእሁድ አጥቢያ ሰዓቱ ከሌሊቱ ስድስት ሰዓት
ሆኗል፤ አሁንም ህማሙን እየታገለ እያላበው በድካም
ለፍጥረቱ ሁሉ ይለምናል፤ “አቤቱ ህዝብህን አድን ርስትህን
ኢትዮጰያንም ባርክ” ይላል። ህመም የጀመረው መጋቢት 3
ዓርብ ቀን ነው፤መታመሙን የሰሙ እንደርሱ ቅዱሳን የሆኑት
ዘርአ ቡሩክ፤ ፍሬ ቅዱስ፤ያዕቆብ፤ብንያምና ዮሴፍ እንዲሁም
በወቅቱ የኢትዮጰያ ንጉስ የነበረው እንድርያስ ሊጠይቁት
ተሰብስበዋል ወደ አጠገቡ መድረስ ግን አልተቻላቸውም
አባታችን ገብረመንፈስ ቅዱስ የሚጋርደው እንጨት ዛፍ
በሌለበት በርሃ እንደ አንበሳ ተኝቶ አዩት በላዩ ያረፈው
የእግዚያብሔር ጸጋ ከፊቱ የሚወጣው ብርሃን ቀይ መልኩ
ረዥም የራስ ጠጉሩ እንደ ነጭ ሐር የሚሆን ጽሕሙ
አስደነቃቸው። ከሌሊቱ ሰባት ሰዓት ሲሆን ከሰማይ ታላቅ
ነጎድጓድ ድምጽ ተሰማ ጌታችን መላአክትን አስከትሎ ወደ
አባታችን ወረደ፤ ከሰማይ ወደ ምድር ህብሩ አምሳያው ልዩ
ልዩ የሆነ እንደ ጸሐይና እንደ ጨረቃ የሚያበራ እንደ
ወንጪፍ ድንጋይ ይወረወር ነበር ከዚያ የነበሩ ሁሉ ፈሩ ወደ
ኃላም ሸሹ ምድር ራደች ተራሮች ኮረብቶች ተናወጡ ብርቱ
ጩኸት
ንውጽውጽታ ሆነ። “ወዳጄ ገብረመንፈስ ቅዱስ ሰላም ላንተ
ይሁን” እነሆ የማይታበል ቃል ኪዳን እገባልኃለው ስምህን
የጠራ መታሰቢያህን ያደረገውን፤ እጣን ቋጥሮ ግብር ሰፍሮ
መባ ይዞ ቤትህ የመጣውን እምርልኃለው አንተ ከገባህበት
ገነት መንግስተ ሰማያት አገባዋለሁ አለው፤ አባታችንም
“አቤቱ ጌታ ሆይ የኢትዮጰያን ህዝብ ማርልኝ” አለው፤ እነሆ
ምሬልኃለው አስራት በኩራት አድርጌም ሰጥቼሃለው፤
ከመጋቢት አምስት ቀን ጀምሮ ዝክርህን ያድርጉ
በአማላጅነትህም ይማጸኑ አለው። ከዚህ በኃላ ሰባቱ ሊቃነ
መላእክት የአባታችንን ነፍስ ሊቀበሉ ወረዱ በታላቅ
ምስጋናም ወደ ሰማይ አሳረጉት ስጋውንም ይዘውት ሄዱ የት
እንደተቀበረ ግን እስካሁን አይታወቅም አንዳንዱ
በእየሩሳሌም ነው ይላሉ፤ ሌላው በምድረ ከብድ ነው ይላል
ግን እስካሁን ልክ እንደ ሊቀ ነብያት ሙሴ ስጋ የት
እንደተቀበረ አይታወቅም። ገድሉ ትሩፋቱ ከሰማይ ከዋክብት
ከምድር አሸዋ ይበዛል ኢትዮጰያን አብዝቶ ይወዳታል፤
ምድራዊ ምግብ አልተመገበም የእናቱን ጡት እንኳን
አልጠባም፤ ልብስ፤ መጠለያ አልፈለገም፤ የክረምት ቁር የበጋ
ሐሩር እየተፈራረቀበት በተጋድሎ 562 ዓመት ኖረ፤ በዛሬዋ
ቀን ሩጫውን ጨረሰ። ለእግዚያብሔር ምስጋና ይሁን
እኛንም ከአባታችን በረከት ያሳትፈን።
አምላከ ገ/መንፈስ ቅዱስ መንገዱን ያብራልን ። ገድሉንም
ሰሚወች ብቻ ሳንሆን እምንማርበት ያድርግልን ።
No comments:
Post a Comment