ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ነኝ

ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ነኝ
ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ነኝ

Tuesday, May 31, 2016

=>+*"+<+>ግንቦት 24<+>+"*+

አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
አሜን
ግንቦት 24-ጌታችን ከቅድስት ድንግል እናቱ፣ ከአረጋዊ ዮሴፍና
ከሰሎሜ ጋር ወደ ግብፅ የተሰደደበት ዕለት ነው፡፡
+ በዚህችም ዕለት ጌታችን በአረጋዊ ዮሴፍ በትር ብዙ አስደናቂ
ተአምራትን አድርጓል፡፡ ዳግመኛም እመቤታችንና የተወደደ
ልጇን መድኃኔዓለምን በእጆቹ ሥራ ይመግባቸው የነበረና
እነርሱንም ከሄሮድስ ለማዳን ብዙ ሰማዕትንት የተቀበለ
ጻድቁና የ83 ዓመቱ አረጋዊ ዮሴፍ ግብፅ የገባበትና ቅዳሴ ቤቱ
የከበረበት ዕለት ነው፡፡
+ ከ12ቱ ደቂቀ ነቢያት አንዱ የሆነው ነቢዩ ቅዱስ ዕንባቆም
ዕረፍቱ ነው፡፡ ቅዳሴ ቤቱም በዚኹ ዕለት ነው፡፡
+ የአሮን ልጅ አልዓዛር ዕረፍቱ ነው፡፡
+ ከእንጽና አገር የተገኘው የከበረ አባት ቀሲስ አብቁልታ
በሰማዕትነት ዐረፈ፡፡
የእመቤታችንና የልጇ የመድኃኔዓለም ስደት-ከገድለ አረጋዊ
ዮሴፍ ላይ የተገኘ፡- የእመቤታችን ስደት የመጀመሪያው የአዲስ
ኪዳን ስደት ነው፡፡ ከገነት የተሰደደውን አዳምን ወደ ቀደመ
ክብሩና መንበሩ ከዚያም ወደ ሚበልጥ ክብር ለመመለስ
የተወለደው ጌታችንና አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ገና
ከሕፃንንቱ ጀምሮ ስደትንና መከራን ተቀብሏል፡፡ ወላዲተ
አምላክ ቅድስት እናቱ እሳትን አዝላ በብርድ ተንገላታለች፣ ለእኛ
የሕይወት እንጀራን ተሸክማ እርሷ ተርባለች፣ የሕይወትን ውሃ
ተሸክማ እርሷ ተጠምታለች፣ የሕይወት ልብስን ተሸክማ ሳለ
እርሷ ተራቁታለች፣ የሕይወት ሀሴት ደስታ ተሸክማ እርሷ
አዝናለች፡፡ እመ አምላክ ስለ ልጇ ብላ ተርባ፣ ተጠምታ፣
ታርዛለች፤ ደክማና አዝና አልቅሳለች፡፡ እግሯ ደምቷል፣ እሾህ
ወግቷት አንቁረው አውጥተውላታል፡፡ እርሷም ይህንን ሁሉ
መከራ የተቀበለችው ልጃን ለማዳንና ለእኛ ለዘላለማዊው
ድኅነት ነውና አባቶች እንዲህ ብለው አመስግነዋታል፡- «ድንግል
ሆይ ርጉም በሆነ ሄሮድስ ዘመን ከልጅሽ ጋር ከሀገር ሀገር
ስትሸሺ ከአንቺ ጋር መሰደዱን አሳስቢ ፤ ድንግል ሆይ ከዓይንሸ
የፈሰሰውንና በተወደደ ልጅሽ ፊት የወረደውንመሪር እንባ
አሳስቢ፤ ድንግል ሆይ ረሀቡንና ጥሙን፣ ችግሩንና ኀዘኑን፣
ከእርሱ ጋር የደረሰብሽንም ጭንቅ ሁሉ አሳስቢ›› ቅዳሴ
ማርያም፡፡
የእመቤታችንን የስደቷን ጥንተ ነገር ስናየው እመቤታችን
በቤተ መቅደስ ሳለች ከአባቷ የሚመጣላትን የትረፈረፈ ሀብት
ለድኆችና ጦም አዳሪዎች ትመጸውት ነበር፡፡ 7 ዓመት በሆናት
ጊዜ ግን ወላጆቿ ዐረፉና እነርሱ የተውላትን ወርቅና ብዙ
ገንዘብ እግዚአብሔርና ለጦም አዳሪዎች ሰጠች እንጂ ምንም
አልወሰደችም፡፡ ካህናቱ እንደ በባሕላቸው መሠረት በቤተ
መቅደስ በብፅዓት ያደገን ሰው (ሴትም ይሁን ወንድ) ለአካለ
መጠን ሲደርስ በቤተ መቅደስ እያገለገለ እንዲኖር ወይም
ከካህናቱ ወገን መርጦ እንዲያገባና ሀብት ሰጥተው እንዲሸኙት
ሁለት ምርጫ ይሰጡታል፡፡ እመቤታችንም 12 ዓመት በሆናት
ጊዜ ሊቀ ካህናቱ ዘካርያስይህንኑ ምርጫ ሲያቀርብላት
እመቤታችንም በልቧ የሰው ልጅ ሀሳብ የላትምና ‹‹እኔስ
በእግዚአብሔር ቤት እያገለገልኩ መኖርን እመርጣለሁ››
አለችው፡፡ ካህናቱም ‹‹ስለእርሷ ወደ ቤተ መቅደስ ገብተህ
እግዚአብሔር የሚነግርህን በጸሎት ጠይቅ›› አሉትና እርሱም
የክህነት ልብሱን ለብሶ ወደ ቅድስተ ቅዱሳኑ ገብቶ በጸሎት
ሲጠይቅ እግዚአብሔር መልአኩን ልኮለት ሚስቶች
የሌሏቸውን የዳዊት ወገን የሆኑ ወንዶችን ሰብስቦ በበትራቸው
ላይ ስማቸውን ጽፎ ወደ ቅድስተቅዱሳኑ እንዲያገባው ነገረው፡፡
ሊቀ ካህናቱ ዘካርያስም በአዋጅ አስነግሮ 1985 ብሮችን
ሰብስቦ ሲጸልይባቸው ቢያደር በአረጋዊ ዮሴፍ በትር ላይ
ምልክት ታየ፡፡ በትሩንም ሲሰጠው ነጭ ርግብ መጥታ በዮሴፍ
ላይ አረፈች፡፡ እርሱም ድንግልን እንዲወስዳት ሲነገረው
አለቀሰ፡፡‹‹ይቅር በሉኝ እኔ ሽማግሌ ነኝና ልጆችም አሉኝ፤
ዕድሜዬም 83 ዓመት ነውና›› እያለ አለቀሰ፡፡ ዘካርያስም
‹‹ይህ ሥራ ከእኛ ዘንድ አይደለም፣ እግዚአብሔር አዞናል
እንጂ፡፡ እነሆ እርሷን ትጠብቃት ዘንድ ሰጥቶሃልና
የእግዚአብሔርን ትእዛዝ እምቢ አትበል፤ ትእዛዙን አንቀበልም
ያሉትን ፈጣሪህ እግዚአብሔር እንዴት እንዳደረጋቸው አስብ…››
እያለ አጽናናው፡፡ አገራዊ ዮሴፍም እየፈራ ድንግል ማርያምን
ወደቤቱ ወሰዳት፡፡ እቤቱወስዶም ልጆቹና ቤተሰቦቹ ይጠብቋት
ዘንድ አደራ ሰጥቷቸው ወደ ንግድ ሄደ፡፡ እመቤታችንም ወደ
ዮሴፍ ቤት በገባች ጊዜ ልጆቹ እናታቸውበልጅነታቸው
ሞታባቸዋልችና የሙት ልጆች ሆነው አገኘቻቸው፡፡ ዮሴፍ
አስቀድሞ ማርያም የምትባል ሚስት አግብቶ ነበር፡፡
ከእርሷም 3 ሴቶችና 4 ወንዶች ልጆች ነበሩት፡፡ እነርም
ስምዖን፣ ያዕቆብ፣ ይሁዳና ዮሳ ናቸው፡፡ ማቴዎስና ማርቆስም
ይህንን በወንጌላቸው ጽፈውታል፡፡
እመቤታችንም በመልአኩ ብስራት ጌታችንን ስትፀንስ ያንጊዜ
ዕድሜዋ 14 ዓመት ከ11 ወር ነበር፡፡ አረጋዊ ዮሴፍም ከ3
ወር በኋላ ሥራውን ጨርሶ ወደ ቤት ሲመለስ ደንግልን ፀንሳ
አገኛትና እጅግ ደነገጠ፡፡ በራሱም ላይ ትቢያን ነስንሶ በምድር
ላይ ወደቆ መራራ ልቅሶን አለቀሰ፡፡ ‹‹ማርያም ሆይ ካህናቱ
ስለ አንቺ ቢመረምሩኝ ምን እመልሳለሁ? በፈጣሪዬ
በእግዚአብሔር ፊትስ እንዴት እቆማለሁ? ከሚያገኘኝ ስድብም
የተነሣ ወዮልኝ፡፡ የእስራኤል ልጅ ሆይ ከማን ፀንስሽ?
ክብርሽንስ የደፈረ ማን ነው?...›› እያለ ጠየቃት፡፡ ድንግልም
‹‹እኔ ንጹሕ እንደሆንኩ እግዚአብሔር ያውቃል፤ ይህን
ያደረገው እግዚአብሔር ነው…›› እያለች ሁኔታውን በደንብ
አስረዳችው፡፡ እርሱም የሚያደርገው ግራ ገብቶት ሳለ
ይገልጥለት ዘንድ በልቅሶ ወደ እግዚአብሔር አመለከተ፡፡
እመቤታችንም ‹‹ጌታዬ ሆይ ይህን ምሥጢር ለአገልጋይህ
ለዮሴፍ ግለጥለት…›› ብላ ጸለየች፡፡ ወዲያውም እግዚአብሔር
ልአኩን ልኮ ለዮሴፍ በሕልም ተነጋገረው፡፡ በማኅፃኗ ያለው
በግብረ መንፈስ ቅዱስ ነውና አትፍራ… ሕዝቡንም ሁሉ
ከኃጢአታቸው ያድናቸዋል…›› እያለ አስረዳው፡፡ ከእንቅልፉም
ነቅቶ እጅግ ደንግጦ ወደ እመቤታችን ቢሄድ ስትጸልይ አገኛትና
ሰገደላት፡፡ ከዚህም በኋላ በናዝሬት ከሚኖሩ ከካህናት ወገን
የሆነ አንድ ካህን አረጋዊ ዮሴፍን ሰላምታ ይሰጠው ዘንድ ወደ
ቤቱ መጥቶ ‹‹ምነው ወደ ቤተ መቅደስ አልመጣህም?››
ቢለው ዮሴፍም ‹‹ከመንገድ የመጣሁት ገና ትናንት ነውና አረፍ
ልበል ብዬ ነው›› አለው፡፡ እንዲህ ሲጨዋወቱ ያም ካህን ወደ
ንጽሕት ደንግል አይኖቹን አንሥቶ ተመለከተና እንደፀነሰች
ዐወቀ፡፡ ወዲያው ሮጦ በፍጥነት ወደ ካህናቱ በመሄድ ‹‹ስለ
እርሱ ምስክር የሆናችሁለት ዮሴፍ እነሆ በደለ፣ ኃጢአትንም
ሠራ፣ ከእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ የወሰዳትን፣ እናንተም
ጠባቂዋ ያደረጋችሁት ድንግል ማርያምን ዐወቃት ፀነሰችም››
ብሎ ነገራቸው፡፡
እነርሱም ወደ ዮሴፍ መልእክተኞች ልከው ‹‹ማርያም ይዘሃት
ና›› ብለው ላኩበት፡፡ የሴፍም አምጥቷት ሁሉም ቢመለከቷት
ፀንሳች፡፡ ወደ ካህናቱም ሁሉ መልአክተኞችን ልከው ሁሉም
ካህናት ተሰበሰቡና ዮሴፍንና ድንግል ማርያምን በአደባባይ
አቆሟቸው፡፡ እመቤታችንንም ‹‹በእስራኤል ደናግል ላይ
ለምን ስድብን አደረግሽ?›› እያሉ ወቀሷት፡፡ በሙሴም ሕግ
መሠረት ሆድን የሚሰነጥቅ ማየ ዘለፋ አጠጧትና
የሚያደርጋትን ለማየት ተሰበሰቡ፡፡ ነገር ግን ማየ ዘለፋው
እንኳንስ በእርሷ ላይ ጉዳት ሊያደርስ ይቅርና ፊቷን እንደ
ሚያዝያ ጨረቃ አደመቀው፡፡ የመንፈስ ቅዱስን ሥራ
የማያምኑትን ብዙዎችን ግን አቃጠላቸው፡፡ እነርሱም
የድንግልን ንጽሕናዋን ባዩ ጊዜ እጅግ ተደነቁ፡፡ ዮሴፍንና
እመቤታችንንም ‹‹እግዚአብሔር ካልፈረደባችሁ እኛ
አንፈርድባችሁ በሰላም ወደ ቤታችሁ ሂዱ›› ብለው
አሰናበቷቸው፡፡
በአውግስጦስ ቄሣር ትእዛዝ መሠረት ሄሮድስ በሀገረ ይሁዳ
ሰው ሁሉ በየወገኑ፣ በየሀገሩ፣ በየአባቱ ይቆጠር ዘንድ አዘዘ፡፡
አይሁድም ለመቆጠር ብቻ ሳይሆን ሄሮድስን አይወዱትም
ነበርና ከቄሣር ጋር ያጣሉት ዘንድ ተሰበሰቡ፡፡ እመቤታችንም
የመውለጃዋ ወቅት ደርሶ ነበርና አረጋዊ ዮሴፍ ወደ ቤተልሄም
ወስዳትና ከአንዲት የእረኞች ዋሻ ውስጥ ይዟት ገባና በዚያ
አደሩ፡፡ በዚያም ከብቶች የሚያድሩበት የፈረሰ ግንብ ነበረ፡፡
ይህም በኬብሮን ትይዩ ሲሆን አቀድሞ የእሴይ ቤት ነበርና
ዳዊት በዚህ ቤት ተወልዷል፣ በዚያም በሳሙኤል እጅ
የመንግሥት ቅባት ተቀብቶበታል፡፡ ቦታው በባቢሎን ስደት ጊዜ
ፈርሶ የፈረሰው ግንብ ከሩቅ ለሚመጡ ነጋዴዎች ማደሪያ ሆኖ
ነበር፡፡ በአጠገቡም ዋሻ ነበርና ጌታችን በታኅሣሥ ወር
በመንፈቀ ሌሊት ማክሰኞ ቀን በዚያ ዋሻ ተወለደ፡፡ ጌታችንም
በተወለደ ጊዜ ዋሻው በእጅጉ ስላበራ ዮሴፍ ደንግጦና
ተንቀጥቅጦ መሬት ላይ ወደቀ፡፡ እመቤታችንም ስትወልድ
እንደሴቶች ሁሉ ልማድ ሕማም አላገኛትም፡፡ መልአኩም
ለእረኞቹ አብስሯቸው ወደ ዋሻው ሄደው የተወለደውን ሕፃን
ከእናቱና ከዮሴፍ ጋር አገኙት፡፡ ከእረኞቹም አንዱ
የቤተልሔሙና በኋላም በይሁዳ ተተካው ማትያስ ነበር፡፡
እረኞቹም የበግ ጠቦትና የላም ወተትን፣ ማርንና ቅቤን
አምጥተው እጅ መንሻ አቀረቡ፡፡ የሕፃኑንም መለኮታዊ እግር
ስመው ከሁሉም በፊት አስቀደመው ሰገዱለት፡፡
ለእመቤታችንና ከዮሴፍም ከሰገዱ በኋላ ተመልሰው ሄደው
በይሁዳ ሀገር ሁሉ ዜናውን ተናገሩ፡፡
ሰሎሜም እመቤታችን በድንግልና የበኩር ልጇን እንደወለደች
ስትሰማ መጀመሪያ ‹‹በዓይኖቼ ካላየሁ በእጆቼም ካልዳሰስኩ
አላምንም›› ብላ ወደ ዋሻው ሄደች፡፡ ወደ እመቤታችንም
ቀርባ ሰውነቷን ዳሰሰች፡፡ ወዲያውም መለኮታዊ እሳት
የወጣበትን ሰውነቷን ዳሥሣለችና እጆቿ ተቃጠሉ፤ ደረቁም፡፡
ወዲያውም በታላቅ ቃል እየጮኸችና እያለቀሰች ‹‹የአምላክ
እናት ሆይ ይቅር በይኝ የሃይማኖቴ ጉድለት ታላቅ መከራ
አመጣብኝ›› እያለች በእመቤታችን ፊት መሪር ልቅሶን
አለቀሰች፡፡ ድንግል ማርያምም ወደ ልጇ ማለደችላት፡፡
በዚህም ጊዜ መልአክ መጥቶ ሰሎሜን ‹‹እግዚአብሔር ይቅር
ብሎሻል፣ ወደ ሕፃኑ ሂጂና በተቃጠሉ እጆቺሽ ያዥውና ታቀፊው
ተድኛለሽ›› አላት፡፡ እመቤታችንም ትታቀፈው ዘንድ ሕፃኑን
ልጇን ሰጠቻት፡፡ ሰሎሜም ታቀፈችው ጊዜ እጇ ወዲያው
ዳነላትና የእመቤታችንን ደንግልናዋን አምና ሰገደችላት፡፡
ሰሎሜም ያየችውንና የሆነውን ሁሉ ለኢየሩሳሌም ነዋሪዎች
ሁሉ ለማውራት እጅግ ተቻኩላ ከዋሻው ወጥታ ስትሄድ ከሰማይ
ድምጽ መጣላትና ያየችውን ተአምር ሕፃኑ ወደ ቤተ መቅደስ
እስኪገባ ድረስ ለማንም እንዳትናገር አስጠነቀቃት፡፡ ጌታቸንም
እንደ አይሁድ ልማድ በ8ኛ ቀኑ ግዝረትን በግብረ መንፈስ
ቅዱስ ፈጽሞ በ40ኛውም ቀን ወደ ቤተ መቅደስ ወሰዱት፡፡
ጌታችን ከመወለዱ ከ277 ዓመት በፊት በንጉሥ በጥሊሞስ
ትእዛዝ 72ቱ ሊቃውንት መጻሕፍቶቻቸውን ከዮናናውያን ቋንቋ
ወደ ጽርዕ ቋንቋ ሲተረጉሙ የ123 ዓመቱ ስምዖን አንዱ
ነበር፡፡ ትንቢተ ኢሳይያስን የተረጎመው እርሱ ነበርና ድንግል
ድንግልና ፀንሳ በድንግልና እንደምትወልድ ይህንንም ሳያይ
እንዳይሞት እግዚአብሔር ቃል ገብቶለት ነበር፡፡ ወደ
መቅደስም ሲመጣ መልአኩ ለስምዖን ተገልጦለት ሲጠብቀው
የኖረው ተስፋው ዕውን ሆኖ ዛሬ መሢሑን በክንዶቹ
እንደሚታቀፈው ነገረው፡፡ በቤተ መቅደስም ጌታችንን
አገኘውና ታቅፎ ‹‹ጌታ ሆይ ዓይኖቼ ማዳንህን አይተዋልና
ባሪያህን ሰላም አሰናብተው›› አለው፡፡ ለእመቤታችንም
‹‹ጦርና ሰይፍ በልብሽ ውስጥ ይገባል›› ብሎ በልጇ ምክንያት
የሚደርስባትን መከራ በትንቢት ነገራት፡፡ ‹‹ጦርና ሰይፍ››
ያለውም የክርስቶስን መከራ ነው፡፡ በሕማሙና በመቸንከሩ
ልቧ መሪር በሆነ የኀዘን ጦር ተወግቷልና አንጀቷም በተሳለ
የሰይፍ ኀዘን ተነዋውቷልና፡፡ ልጇ የተቀበላቸው መከራዎችንም
እንደ እርሱ በልቡናዋ እመቤታችንም ተቀብላቸዋለችና
ስለዚህም የሰማዕታት እናት ትባላለች፡፡
ከሰብዓ ሰገል አንዱ ዘሮአስተር የሚባለው ስለ ኮከብ መውጣትና
ስለ ክርስቶስ ትንቢት ተናግሮ ነበርና ከዚያ ጊዜ ጀምሮ የጥበብ
ሰዎች መጻሕፍትን ተምረው በትንቢቱም ታምነው ይኖሩ
ነበር፡፡ ስለዚህም በየዓመቱ ሁሉም አንድ ቀን ከፍ ባለ ተራራ
ላይ ይሰበሰቡና ኮከቡን ይመለከቱታል፡፡ ክርስቶስም በተወለደ
ጊዜ አዲስ ኮከብ በሕፃን መልክ ታያቸው፡፡ በላዩም የመስቀል
ምልክት አለው፡፡ ‹‹የአሕዛብ ተስፋቸውና መስፍናቸው፣
የአይሁድ ንጉሣቸው ወደ ምድር ወረደ›› የሚል ቃልም ሰሙ፡፡
‹‹እጅ ለመንሳትና ለመስገድም ፈጥናችሁ ሂዱ›› አላቸው፡፡
መጽሐፍ ቅዱስ የጥበብ ሰዎችን ቁጥር ባይገልጸውም
አውግስጦስና ዮሐንስ አፈወርቅ 12 ናቸው ብለዋል፡፡ በሦስት
የትውልድ ቅርን መስለው ሦስት ናቸው የሚሉም አሉ፡፡
ዮሐንስ አፈወርቅ እንደተናገረው በ5 ወር ደርሰው ደብረ ዘይት
እግር ሥር ከተሙ፡፡ ተጉዘውም ኢየሩሳሌም ከተማ ገብተው
‹‹የተወለደው የአይሁድ ንጉሥ የት ነው?›› ብለው ሲጠይቁ
ሄሮድስና መላዋ ኢየሩሳሌም ታወኩ፡፡ ሰብዓ ሰገልም በኮከቡ
ተመርተው ወደ ቤተልሔም ዋሻ ገብተው ሕፃኑን ከእናቱና
ከዮሴፍ ጋር አገኙትና ወድቀው ሰገዱለት፡፡ እጅ መንሻቸውን
አቀረቡለት፡፡ መልአኩም ከሄሮድስ እንዲሰወሩ ነግሯቸው በሌላ
መንገድ ተመለሱ፡፡ እመቤታችንና ዮሴፍም ሥርዓቱን ሁሉ
ፈጽመው ሲጨርሱ ወደ ሀገራቸው ተመለሱ፡፡ የስምዖንም
ትንቢት ይፈጸም ዘንድ የሄሮድስ ቁጣ ነደደችና 2 ዓመትና ከዚያ
በታች ያሉ ሕፃናት ሁሉ ይገደሉ ዘንድ አዘዘ፡፡ የነቢዩ
ኤርሚያስም ትንቢት ተፈጸመችና 144 ሺህ ሕፃናትም ተገደሉ፤
መቃብራቸውም በራማ ሀገር በበለስ ዛፍ ሥር ነው፡፡
መልአኩም ለዮሴፍ ተገልጦለት ‹‹ሄሮድስ ሕፃኑን ሊገድለው
ይፈልገዋልና ተነሥ ሕፃኑንና እናቱን ይዘህ ወደ ግብፅ ሽሽ››
አለው፡፡ እርሱም ወዲያው በሌሊት ተነሥቶ ይዟቸው ሸሸ፡፡
ከናዝሬት ጀምረው የባሕሩን ዳርቻ ይዘው እስከ ፍልስጤም
ደረሱ፡፡ በ6ኛው ቀን ደክሟቸው አንድ ዋሻ ውስጥ ገቡ፡፡
እመቤታችንም በጸሎቷ ውኃን አመነጨችና ጠጡ፡፡ ያም
ምንጭ ስሙ የማርያም ውኃ ተብሎ እስከዛሬ አለ፡፡
በሌሎችም ቦታዎች እመቤታች ስትጸልይ ውኃ እየፈለቀ
በእርሱ ልጇን ገላውን ታጥበዋለች፡፡ ዐሥር ቀን ያህል በይሁዳ
ሀገር፣ ዐሥር ቀን ያህል በምድረ በዳ እጅግ አስቸጋሪ ጉዞ
ከተጓዙ በኋላ ግብፅ ደረሱ፡፡
ጌታችንም ምድረ ግብፅ በደረሰ ጊዜ በነቢዩ ኢሳይያስ ትንቢት
መሠረት የግብፅ ጣዖታት ከመሠረታቸው ተነዋውጠው ምድር
አፏን ከፍታ ዋጠቻቸው፡፡ በግብፅ ኤሌዎጶሊዎስ ሀገር ገብተው
ዮሴፍ ማረፊያ ሠራ፡፡ በዚያም ባለች ተራራ ሥር ጌታችን ውኃን
አፈለቀ፡፡ ይህችውም በእኛና በቅብጥ ሰዎች ዘንድ ሰኔ 8 ቀን
የምትታሰበው ዕለት ናት፡፡ ደም ማፍሰስ የለመደ ርጉም ሄሮድስ
ሚስቱን ማርያናንም ከገደላት በኋላ ይበቀሉኛል በማለት
ከእርሷ የወለዳቸውን የገዛ ልጆቹንም ገደላቸው፡፡ ከዚህም
በኋላ በሥጋው ጽኑ መከራ መጣበትና እግዚአብሔር የደዌውን
ዘመን አስረዘመበት፡፡ ቢበላ ቢበላ ይጠግብም
ይልቁንምረሀብና ጥም ይበዛበታል፣ አንጀቱም ተቋጠረ፣
ሰውነቱም ተልቶ ሰው ሁሉ አልቀርበው አለ፡፡ ማቆ ሲያበቃ
በመጨረሻም ክፉ አሟሟት ሞተ፡፡ የእግዚአብሔርም
መልአክ ዮሴፍን ሄሮድስ ስለሞተ ሕፃኑንና እናቱን ይዞ ወደ
እስራኤል እንዲመለስ ነገረው፡፡ ተመልሰውም በፍልስጤም
አልፈው ድልማጥያ ወደምትባል አንዲት ገር ደርሰው በበረሃ
ውስጥ ተቀመጡ፡፡
እመቤታችንም ከነልጇ ረሃቡ ቢጠናባት ትዕማን ወደምትባል
አንዲት ከበርቴ ባለሀብት ቤት ሄዳ ቁራሽ እንጀራንና ለልጇም
ጥቂት ወተትን ለመነቻት፡፡ ያቺ ክፉ ሴት ግን ልብን በሀዘን
የሚሰብር ክፉ ንግግርን ተነጋረቻት፡፡ ጻድቅ ዮሴፍም
‹‹እንግዳን ካለ ይሰጡታል ከሌለ በሰላም ይሸኙታል እንጂ
ለምን ክፉ ንግግርን ትናገሪያታለሽ›› እያለ ሲነጋገሩ አሽከሯ
ኮቲባ የእመቤቷን ቁጣ ሰምታ መጥታ ጌታችንን ከመሬት ላይ
ጥላ እንደ ድንጋይ አንከባለለችው፡፡ እመቤታችንም ደንግጣ
እያለቀሰች ልታነሣው ስትል ዮሴፍ ‹‹ተይው አታንሽው ኀይሉን
ያሳይ›› አላት፡፡ ያንጊዜም ምድር አፏን ከፍታ ዋጠቻት፣ ገረዷ
ኮቲባም በለምጽ ተመታች፡፡ በቤታቸውም ውስጥ በሕይወት
የቀረ የለምና ቤተሰቦቿ ጦጣ ሆነው ከተራራ ወደ ተራራ ሸሹ፡፡
እመቤታች፣ ዮሴፍና ሰሎሜም በትዕማን ቤት 6 ወር
ከተቀመጡ በኋላ መልአኩ ተገልጦ ከዚያ እንዲወጡ አዘዛቸውና
ወጡ፡፡ አርዲስ ወደምትባል ሀገርም ደርሰው የሀገሪቱ ሰዎች
በሰላም ተቀብለው አስተናገዷቸው፡፡ እመቤታችንም ከሀገረ
ገዥው ሆድ ውስጥ በጸሎቷ እባብ ላወጣችለትና ከሕመሙ
ስላደ በጣም አከበሯቸው፡፡ ዕውሮችን፣ አንካሶችን፣
ለምፃሞችንና አጋንንት ያደሩባቸውን ሁሉ እያመጡላት የልጇን
እጆች ይዛ ከሩቅ እያማተበች ፈወሰቻቸው፡፡ ሄሮድስም
እንደሚያፈላልጋቸው መልአኩ ሲነግራቸው ከአንዱ ሀገር ወደ
ሌላው ሀገር እየተዘዋወሩ ታችኛው ግብፅ ንሂሳ ድረስ ደረሱ፡፡
እመቤታችንም በዚያ ያሉ ሕመምተኞችን ፈወሰችላቸው፡፡
ከዚህም በኋላ አሁንም መልአኩ ነግሯቸው ደመናም መጥታ
ነጥቃ ወሰደቻቸውና የ38ቱን ወራት መንገድ በአንድ ጊዜ
አደረሰቻቸው፡፡ በዚያም ትንሽ ከቆዩ በኋላ ወደ ቤጎር ቆላ
ደረሱ፡፡ በዚያም ግብፃውያን እንደ ሕጋቸው ለአማልክቶቻቸው
ላሞችን አርደው ሠውላቸው፡፡ በጎሽ፣ በአውራሪስ፣ በነጭ
ዝንጀሮ የሚመሰሉ አጋንንትም መጡ፡፡ እመቤታችንም ከሩቅ
ሆና ተመልክታቸው እነዚያን አጋንንት በጸሎቷ እንደጢስ
በተነቻቸው፡፡ ግብፃውያንም ፈርተው እየጮኹ ሸሹ፡፡ በዚያም
ወራት ‹‹ረዳት አማልክቶቻችንን ጠፉብን›› ብለው እያዘኑ ሳለ
ዮሴፍን ሲጸልይ አግኝተውት አስረው በምድር ላይ አስተኝተው
40 ግርፋት ገረፉት፡፡ እርሱም በዚህ ጊዜ ‹‹እመቤቴ ሆይ ስለ
አንቺና ስለ ልጅሽ ይህ መከራ አግኝቶኛልና እርጂኝ›› ብሎ
በኀይል ጮኸ፡፡ እመቤታችንም ድምጹን ስትሰማ የሄሮድስ
ጭፍሮች የመጡ መስሏት እጅግ ደነገጠች፡፡ ቅዱስ
ገብርኤልም ተገልጦ ካረጋጋት በኋላ ዮሴፍን በኀይል ይደበድቡ
የነበሩትን በእሳት ሰይፉ ጨረሳቸው፡፡ ዮሴፍንም በእጆቹ
ዳሰሰውና ፈወሰው፡፡ እመቤታችንም ዮሴፍን ባየችው ጊዜ
‹‹ይህ ሁሉ መከራ ያገኘህ በእኔና በልጄ ምክንያት ነው››
ብላውአንገት ለአንገት ተቀቅፈው ተላቀሱ፡፡ መልአኩም ‹‹ይሄ
ሀዘናችሁ በደስታችሁ ጊዜ ይረሳል…›› እያለ አረጋጋቸውና
ዐረገ፡፡
የሀገሩ ሰዎችም ይወጓቸው ዘንድ ወጡና ክፉ ውሾችን
ለቀቁባቸው፡፡ ነገር ግን ውሾቹ በሰው አንደበት እመቤታችንን
እያነገሯት ሰግደው የእግሯን ትቢያ ልሰው በመመለስ
ባለቤቶቻቸውን መልሰው መናከስ ጀመሩ፡፡ ብዙዎቹንም
ገደሏቸው፡፡ ዮሴፍም ‹‹እመቤቴ ሆይ በዚህ ሀገር ከምንኖርስ
በዱር በበረሀ ብንኖር ይሻለናል›› ብሏት ወደለሌላ ትርጓሜዋ
የሰላም ሀገር ወደሆነች ዲርዲስ ሀገር ደረሱ፡፡ ሰዎቹም
‹‹ይህችስ የነገሥታት ወገን ትመስላለች በላያችን ላይ
ትነግሥብናለች›› ብለው በክፉ ሲነሱባቸው በማግስቱ ደመና
ነጥቃ ወስዳ ኤልሳቤጥ በሞት ካረፈችበት በረሀ አደረሰቻቸው፡፡
ዮሐንስ በእናቱ በድን ላይ ሆኖ እያለቀሰ ሳለ ዮሴፍንና ሰሎሜን
ባያቸው ጊዜ ደነገጠ፡፡ ጌታችንም አረጋጋው፡፡ እመቤታችንም
ስለ ኤልሳቤጥ ሞት እጅግ መሪር የሆነ ልቅሶን ስታለቅስ ልጇ
ድንቅ ምሥጢርን ከነገራት በኋላ አረጋጋት፡፡ እመቤታችንም
‹‹እናቱ ሞታበታለችና በዚህም በረሀ ማንም የለመውና
ዮሐንስን ከእኛ ጋር እንውሰደው›› ስትለው ጌታችን ‹‹ዕድሉ
በዚህ በረሀ ነው›› ብሎ አረጋጋት፡፡ ከዚህም በኋላ ደመና ነጥቃ
ወስዳ ወደ ጋዛ ምድር አደረሰቻቸውና በዚያ አተር የሚያበራዩ
ሰዎችን አግኝታ እመቤታችን ‹‹ለልጄ አተር ስጡኝ››
አለቻቸው፡፡ እነርሱም ክፉዎች ነበሩና ‹‹ይህ አተር ሳይሆን
ድንጋይ ነው›› አሏት፡፡ ሕፃኑ ልጇም ‹‹እናቴ ሆይ እንደቃላቸው
ይሁንላቸው ተያቸው›› አላት፡፡ ያንጊዜም አተሩ ድንጋይ ሆነ፣
ይህም እስከዛሬም ድረስ አለ፡፡ ከዚህም በኋላ እመቤታችን ወደ
ተወለደችበት ሀገር ወደ ሊባኖስ ተራራ ሄደው በዚያ ያሉ
ሰዎችም በሰላም ተቀበሏቸው፡፡ እመቤታችንም ብዙ
ተአምራት አደረገችላቸው፡፡ ገዥው ደማትያኖስም ሄሮድስን
ሊወጋው ጦሩን አዘጋጅቶ ሳለ ነገር ግን ፈቃደ እግዚአብሔር
ከለከለችው፡፡ መልአክም ተገልጦለት በእርሱ ምክንያት ብዙ
ሰማዕታት ይሰየፉ ዘንድ አላቸውና ጊዜው ገና መሆኑን
አስረድቶት ሄሮድስን በጦር እንዳይገድለው ከለከለው፡፡
ደማትያኖስም ኃይሉና ጦሩ እጅግ የበረታ ነበር፡፡ ቅዱስ ጊጋርም
በዚህ ወቅት ስለ እመቤታችንና ስለልጇ ሰማዕት ሆነ፡፡ ቅዱስ
ገብርኤልም ለእመቤታችን ተገልጦ ወደ ግብፅ እንድትሄድ
ነገራት፡፡ ዳግመኛም መልአኩ ለገዥው ለደማትያኖስ
ተገልጦለት ትንቢቱ ይፈጸም ዘንድ እንዲያሰናብታት ነገረው፡፡
እርሱም አስቀድሞ ‹‹በዙፋኔ ተቀመጪ እኔና ሚስቴ
አገልጋይሽ እንሁን እንጂ ከዚህስ አትሄጂም›› ብሎ ግድ ብሏት
ነበርና፡፡ ከዚህም በኋላ የአንድ ቀን መንገድ ሸኝቷት እንዲህ
አላት፡- ‹‹እመቤቴ ሆይ ሄሮድስ ቢፈልግሽ ወደኔ መልእክት
ላኪብኝ ፈጥኜ እመጣለሁ፡፡ የእስራኤል አምላክ ቢፈቅድልኝ
ከዛብሎን፣ ከንፍታሌምና ከሐሴቦን ጀምሮ ይሁዳንና
ኢየሩሳሌምን ሁሉ አጠፋቸዋለሁ፡፡ ሰውን ብቻ የምገድል
አይደለሁ ዛፎቻቸውን ቆመው እንዲታዩ አልፈቅድም፡፡
ሀገሪቱንም ፍርስራሽ አደርጋታለሁ›› አላት፡፡ ይህ
የእግዚአብሔር ፈቃድ እንዳልሆነ አስረድታው መርቃ
አሰናበተችውና በበነጋታው ተለያዩ፡፡
ወደ ቤተልሔምም ከደረሱ በኋላ አሁንም መልአኩ አዘዛቸውና
በሌሊት ተነሥተው ወደ ግብፅ ተጓዙ፡፡ ሄሮድስም ሀገሪቱን
መጥቶ ከበባት፡፡ እነርሱንም ቢያጣ በዚያ ያገኘውን ሁሉ ሰየፈ፡፡
2 ዓመትና ከዚያ በታች ያሉ ሕፃናትን ሁሉ ሰብስበው
እንዲያመጡአቸው አዘዘና 144 ሺህ የቤተልሔም ሕፃናትን
ከእናቶቻቸው ላይ እየቀማ ሰየፋቸው፡፡ መላእክትም እጅግ
ደንግጠው ይህ ለምን እንዲሆን ፈቀድክ ብለውም
አምላካቸውን ጠየቁ፡፡ እንዲህ የሚል ቃልም ከዙፋኑ ወጣ፡-
‹‹ኢየሩሳሌም በሰው ደም እንደምትታጠብ በነቢያት እንዲሁ
ተጽፏልና እነዚህ ሕፃናት ለመንግሥተ ሰማያት ቀድመው
ተዘጋጁ ናቸው›› እመቤታችንና እነ ዮሴፍም ግብፅ ደርሰው
በዚያ ቢቀመጡም ነገርን ግብፅ አልተመቸቻውም፡፡ ሕዝቡም
በሰላም አልተቀበላቸውም፡፡ ወደ ኢትዮጵያ በመጡ ጊዜ ግን
ሕዝቡ ሁሉ በሰላም ተቀበላቸው፡፡
ከመንገዱና ከርሃብ ጥሙ ጽናት የተነሣ እጅግ ደክማለችና
የኢትዮጵያ ሰዎች እመቤታችንን አይተው እጅግ አዘኑላት፡፡
‹‹ይህችስ የነገሥታት ዘር ትመሥላለች ነገር ግን አንዳች ችግር
አጋጥሟት ተሰዳ ወደ ሀገራችን መጥታለች..› ብለው
እንክብካቤን አደረጉላት፡፡ እግራቸውን አጥበው በክብር
ማረፊያዎች ላይ አሳረፏቸው፡፡ መልካም መስተንግዶም
አደረጉላቸው፡፡ እመቤታችንም ከድካሟ ካረፈች በኋላ ሀገሪቱን
በእጅጉ ወደደቻትና የተወደደ ልጇን ‹‹ይህን ሀገርና ሕዝቧን
በመላ ወድጃቸዋልሁና በዚህ እስከ መጨረሻው እንኑር››
አለችው፡፡ ጌታችንም ክብርት እናቱን ‹‹ይህች ቅድስት ሀገር
ናት፣ በኋለኛው ዘመን የቅዱሳን መነኮሳት ቦታ ትሆናለች፡፡
በውስጧም እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ እመሰገንባታለሁ፤
የአንቺም ስም ሳይጠራ አይውልባትም›› አላት፡፡ ከዚህም በኋላ
ጌታችን ደመና ጠቅሶ በእርሷ ላይ ተቀመጡ፡፡ መልአኩ ቅዱስ
ዑራኤልም መጣና እየመራቸው መላ ኢትዮጵያን ጎበኟት፡፡
እመቤታችንም ሀገሪቱንና ሕዝቦቿን ወዳቸዋለች ደስም
ተሰኝታባቸዋለችና ጌታችን ለክብርት እናቱ ‹‹ይህችን ቅድስት
ሀገር አሥራት አድርጌ ሰጠሁሽ›› አላት፡፡ እመቤታችንም እጅግ
ተደስታ ‹‹ልጄ አምላኬ›› ብላ አመሰገነችው፡፡ ከዚህም በኋላ
ከአብዱ ቦታ ወደ አንዱ ቦታ እየተዘዋወሩ መላዋ ኢትዮጵያን
በኪደተ እግራቸው ባረኳት፡፡
ጌታችንም ‹‹በዚህ ቦታ እንዲህ ዓይነት ቤተ ክርስቲያን
ይታነጻል፤ እከሌ የሚባል እንዲህ ዓይነት ቅዱስ ይነሣል…››
እያለ ብዙ ምሥጢራትን ለእናቱ ነገራት፡፡ ከዚህም በኋላ የስደቱ
ዘመን ሲያልፍ ሄሮድስም በመጨረሻ ክፉ አሟሟትን ሲሞት
መልአኩ ወደ ገሊላ አውራጃ እንዲመለሱ ነገራቸው፡፡
እመቤታችንም ‹‹ከዚህች ሀገርስ ባንሄድ እመርጣለሁ›› ስትል
የተወደደ ልጇ ‹‹እናቴ ሆይ ጽድቅንና ፈቃድን ሁሉ ልንፈጽም
ይገባናል›› ብሎ አጽናናትና ወደ ሀገራቸው ተመልሰው ሄዱ፡፡
እመቤታችን ልጇን መድኃኔዓለምን ይዛ ለምን ተሰደደች?
1ኛ.ትንቢተ ነቢያትን ለመፈጸም፡- እግዚአብሔር ሊያደርግ
ያሰበውን ፈቃዱን ሁሉ ለሰው ልጅ እየገለጠ ነቢያትን ትንቢት
እያናገረ መምህራንን እየላከ መጽሐፍትን እያጻፈ መሆኑን ልብ
ማለት ተገቢ ነው፡፡ ‹‹እግዚአብሔር ለህዝቡ በመጽሐፍ
ይናገራቸዋል››፣ ‹‹በቀንና በሌሊት ባሪያዎቼን ነቢያትን ሁሉ
ልኬባቸው ነበር፣ አዎ ልኬባቸዋለሁ›› እንዲል፡፡ መዝ 87:6፣
ኤር 7፡25፡፡ ከነዚህም ትንቢታት መካከል ስለ እመቤታችንና
ስለ ልጇ ስደት ሲሆን ነቢዩ ኢሳይያስ 19፡1 ላይ ‹‹እነሆ
እግዚአብሔር በፈጣን ደመና እየበረረ ወደ ግብጽ ይመጣል››
በማለት ሲናገር ከሙሴና ከአሮን ጸሎት የተነሳ የግብጻውያን
የእጃቸው ሥራ መጥፋቱን፣ እግዚአብሔር በናቡከደነጾር አድሮ
ወደ ግብጽ መምጣቱን፣ ጣዖታትን ማጥፋቱን የተነበየበት
ከመሆኑ በላይ በእመቤታችን ጀርባ ታዝሎ በፈጣን ደመና
በተመሰለች ከእመቤታችን ጋር ወደ ግብጽ ተሰደደ፡፡ ሊቃውንት
እመቤታችንን ሲመስሏት ደመና ኢሳይያስ የሚሏትም ስለዚህ
ነው፡፡
በዚህ ትንቢት ላይ እንደተገለጸው ግብጽ በጣዖታት የተሞላች
በመሆኗ የጌታችን ስደት በግብጽ ያሉ ጣዖታትን ለማጥፋት
እንዲሆን ተጠቅሷል፡፡ ግብጻውያን ከጥንት ጀምሮ የላም፣
የፍየል፣ የአንበሳ ምስልን በመቅረጽ ያመልኩ ነበር፡፡ እነዚህን
ለማጥፋት የጌታ ስደት ወደ ግብጽ ይሆን ዘንድ ትንቢት አናገረ፡፡
ከዚህም ባሻገር በኛ ሕይወትም ውስጥ ጌታችንን ለመቀበልና
ሥራ እንዲሠራብን በቅድስና ለመኖር የልብን ጣዖታት ማጥፋት
ማጽዳት ይገባል፡፡ ጌታንና ጣዖትን በልባችን ማኖር
አንችልም፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹ብርሃንም ከጨለማ ጋር ምን
ኅብረት አለው? ክርስቶስ ከቤልሆር ጋር መስማማት አለው
ወይስ የሚያምን ከማያምን ጋር ምን ክፍል አለው
ለእግዚአብሔር ቤተ መቅደስም ከጣዖት ጋር ምን መጋጠም
አለው፡፡ እኛ የሕያው እግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ነንና›› ያለው
ለዚሁ ነው፡፡ ቅዱስ ዳዊት መዝ 83፡3 ‹‹ወፍ ለእርስዋ ቤትን
አገኘች ዋኖስም ጫጭቶችዋን የምታኖርበት ቤት አገኘች››
በማለት ሲተነብይ ወፍ ለእርስዋ ቤትን አገኘች ሲል ነቢያት
የተነበዩት ፍጻሜውን በእመቤታችን ማግኘቱን አንድም
እመቤታችን በስደት ግብጽ መኖርያዋ ማድረጓን ዋኖስም
ጫጭቶችዋን የምታኖርበት ሲል ዮሴፍና ሰሎሜም
የሚኖሩበት ቤት ማግኘታቸውን ተናገረ፡፡ ለእመቤታችን
ማደሪያ ጠፍቶ ማደሪያዋን ግብጽ ማድረጓን ተንብየዋል፡፡ ነቢዩ
ሆሴዕ ‹‹እስራኤልን ሕጻን በነበረ ጊዜ ወደድኩት ልጄንም
ከግብጽ ጠራሁት›› እንዳለ (11፡1) እስራኤል በግብጽ ሳሉ
እንደተመረጡ ከዚያም አገር አውጥቶ መንግስት ይሆኑ ዘንድ
እንዳበቃቸው የተናገረበት ትንቢት ከመሆን ጋር የጌታችን ወደ
ግብጽ መሰደድ ሔሮድስ እስኪሞት በዚያ መቀመጡን ከዚያም
መመለሱን የሚያመለክት መሆኑን ቅዱስ ማቴዎስ የነቢዩን
ቃል ፍጻሜ አድርጎ ተናግሯል፡፡ ማቴ 2፡15፡፡
2ኛ. የቅዱሳንን ስደት ለመባረክ ጌታችን ከድንግል እናቱ ጋር
ተሰደደ፡-የክርስትና ሕይወት የመስቀል ላይ ጉዞ በመሆኑ
ክርስቶስን አምነው ለተከተሉት ሁሉ በመከራና በስደት
እንደሚያልፍ ጌታችን ኢየሱስ ክርሰቶስ ከአለም ተመርጠው
ለተከተሉት ደቀ መዛሙርቱ ሲያስተምር ‹‹እኔን መከተል
የሚወድ ቢኖር ራሱን ይካድ መስቀሉንም ተሸክሞ ይከተለኝ››
በማለት ተናገረ፡፡ ማቴ. 16፡24፡፡ በዚህም ቃል መሠረት
ከቅዱሳን ሐዋርያት ጀምሮ የተነሡ ክርስቲያኖች በብዙ መከራ
ውስጥ አለፉ በበረሃ ተሰደዱ፣ በዱር በገደሉ ተቅበዘበዙ በሰይፉ
ተተረተሩ፣ በድንጋይ ተወገሩ፡፡ ዛሬም ቢሆን በእምነት
የተሰደድን የተጨነቅን የምንጸልየው ስደትን ከኛ በፊት
በሕጻንነቱ በቀመሰ ስደትን በሚያውቅ አምላክ ፊት ነው፡፡
3ኛ.ጣኦታተ ግብጽን ለማጥፋት ተሰደደ፡- ግብጽ ከነገሥታቶቿ
ጀምሮ ጣኦትን የሚያመልኩ አሕዛብ የነበሩ ህዝቦች ነበሩ፡፡
እነዚህ ጣኦታት ደግሞ የእንስሳትን ምስል በማስመሰል ደንጊያ
ጠርበው እንጨት አለዝበው ማዕድን አቅልጠው የበሬ፣ የላም፣
የአንበሳ፣ የወፍ ምስል አስቀርጸው ያመልኩ ስለነበር ከተማዋ
በጣኦታት የተሞላች ነበር፡፡ ለዚህም ጌታችን ጣኦታትን
ሊያፈርስ ወደ ግብጽ ተሰደደ፡፡ ገና ከተማዋ ሲገባ በጣኦታቱ ላይ
ያደሩ አጋንንት ጮኸው ወጡ፣ ጣኦታቱም ተሰባበሩ፡፡
4ኛ.ጌታችን ሰው መሆኑን ለመግለጽ ተሰደደ፡- ኢየሱስ ክርስቶስ
አገሩን ሳይለቅ ከሄድሮስ ዓይን መሠወር ይችል ነበር፡፡ ነገር
ግን በአምላካዊ ጥበቡ ከሄሮድስ ዓይን ተሰውሮ ቢሆን ሥጋ
መልበሱ ሰው መሆኑን አይገለጽም ነበር፡፡ በሄሮድስ ዓይን
የማይታይ ከሆነ ሥጋ ሳይለብስ የለበሰ መስሎ የተገለጸ ሥጋና
አጥንት የሌለው (ምትሐት) ነው በተባለም ነበር፡፡ ከአዳም
አካል አንድም ያልጎደለው ሙሉ ዳግማዊ አዳም መሆኑን እና
የለበሰው ሥጋ የሚደማ የሚቆስል በሰይፍም ሆነ በጦር ቢወጋ
ጉዳት የሚደርስበት ሰብአዊ ባሕርይ ያለው መሆኑን
ለማስረዳት ስደተኛ ሆነ፡፡ ሥጋ የለበሰ ሁሉ ከጠላቱ ማምለጥ
የሚችለው ከጠላቱ ፊት ዞር በማለቱ እና በመሸሹ ስለሆነ
ጌታም ከጠላቱ ከሄሮድስ ለማምለጥ ሰው እንደመሆኑ ወደ
ግብጽ ሸሸ፡፡
5ኛ. ምሳሌውን ለመፈጸም ተሰደደ፡- ጌታችን የሥጋ አባቶቹ እነ
አብርሃም፣ ያዕቆብ፣ ኤርምያስ ሁሉ አስቀድመው ወደ ግብጽ
ተሰደው ስለነበር፡፡
6ኛ.ጌታችን የግብፅና የኢትዮጵያ ገዳማትን ይቀድስ ዘንድ
ከድንግል እናቱ ጋር ተሰደደ፡፡
7ኛ.የአዳምን ስደት በስደቱ ለመካስ ጌታችን ተሰደደ፡፡
8ኛ.ዲያብሎስን ለማሳደድ ተሰደደ፡- አዳም ዕፀ በለስን በልቶ
ከፈጣሪው ጋር ተጣልቶ ከገነት ከወጣ በኋላ የእግዚአብሔርና
የሰው ግንኙነት የተራራቀ ሆነ፡፡ ይህን የፈጣሪና የፍጡር
መራራቅ ያመጣው ዲያብሎስ የአዳምን ልጆች ሁሉ
ተቆጣጠራቸው፡፡ ልባቸውን በፍቅረ ጣኦት ሸፍኖ አምልኮተ
እግዚአብሔር እንዳያዩ አደረጋቸው ብዙ የአዳም ልጆችም
የአግዚአብሔርን ፈቃድ ሳይሆን የሰይጣንን ፈቃድ ሲፈጽሙ
ኖሩ፡፡ ጌታም ‹‹አሁን የዚህ ዓለም ገዥ ወደ ውጪ
ይጣላል›› (ዮሐ12፡31) በማለት ሰይጣን ዓለሙን
ተቆጣጥሮት እንደነበረ ይገልጻል፡፡ እግዚአብሔር ወልድ
የሰውን ሥጋ በለበሰ ጊዜ የፈጣሪና የፍጡር ግንኙነት እንደገና
ተመሠረተ፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ዲያብሎስን ከተቆጣጠረው
ከሰው ልቡና አስወጣው ጌታ ከሄሮድስ ፊት እየራቀ ሲሄድ
ያብሎስም ከሰው ፊት እየራቀ ሄደ፡፡ ጌታችን የሚቀበለው
መከራ ሁሉ ዲያብሎስን በርቀት የሚመታ መሣርያ ነበር፡፡
መጨረሻም በመስቀል ላይ የሆነው የጌታችን ሞት
የዲያብሎስ ሞት ሆነ፡፡

=>+*"+<+>አቡነ_ተክለሀይማኖት<+>+"*+

#አቡነ_ተክለሀይማኖት
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን::
እነርሱ በእምነት መንግሥታትን ድል ነሡ፥ ጽድቅን አደረጉ፥
የተሰጠውን የተስፋ ቃል አገኙ፥ የአንበሶችን አፍ ዘጉ፥ የእሳትን
ኃይል አጠፉ፥ ከሰይፍ ስለት አመለጡ፥ ከድካማቸው በረቱ፥
በጦርነት ኃይለኞች ሆኑ፥ የባዕድ ጭፍሮችን አባረሩ። ሴቶች
ሙታናቸውን በትንሣኤ ተቀበሉ፤ ሌሎችም መዳንን ሳይቀበሉ
የሚበልጠውን ትንሣኤ እንዲያገኙ እስከ ሞት ድረስ
ተደበደቡ፤ሌሎችም መዘበቻ በመሆንና በመገረፍ ከዚህም
በላይ በእስራትና በወኅኒ ተፈተኑ፤ በድንጋይ ተወግረው ሞቱ፥
ተፈተኑ፥ በመጋዝ ተሰነጠቁ፥ በሰይፍ ተገድለው ሞቱ፥ ሁሉን
እያጡ መከራን እየተቀበሉ እየተጨነቁ የበግና የፍየል ሌጦ
ለብሰው ዞሩ፤ዓለም አልተገባቸውምና በምድረ በዳና በተራራ፥
በዋሻና በፍርኩታ በምድር ጕድጓድም ተቅበዘበዙ። ዕብ.11፡
33-40
ስለ አምላካቸውም ሲሉ ሁሉን ትተው፣ ሁሉን ንቀው
አምላካቸውን እንደተከተሉ መጽሐፍ ቅዱሳችን ያስረዳል።
ነፍሱን ሊያድን የሚወድ ሁሉ ያጠፋታል፤ ስለ እኔ ግን ነፍሱን
የሚያጠፋ ሁሉ ያገኛታል። ሰው ዓለሙን ሁሉ ቢያተርፍ
ነፍሱንም ቢያጐድል ምን ይጠቅመዋል? ወይስ ሰው ስለ ነፍሱ
ቤዛ ምን ይሰጣል? የሰው ልጅ ከመላእክቱ ጋር በአባቱ ክብር
ይመጣ ዘንድ አለውና፤ ያን ጊዜም ለሁሉ እንደ ሥራው
ያስረክበዋል።(ማቴ.16፡ 25-27
ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊትም ስለቅዱሳኑ ሲናገር፤
“እግዚአብሔር በቅዱሳኑ ላይ ድንቅ ነው።” ይላል። መዝ.
67/68፡35
ስለ ጽድቅ የሚራቡና የሚጠሙ፣ እንዲሁም የሚሰደዱ ብጹዓን
ናቸው ይጠግባሉና፣ መጽናናትንም ያገኛሉና…+++ ጌታ በተራራ
ስብከቱ ከተናገራቸው፣ ካስተማራቸው የሕይወት ምግብ የሆነ
ቃሉ በማቴ.5፡1-ፍጻሜ
እግዚአብሔር አምላካችን ሰማዕታትን በደም፤ ቅዱሳንን
በገዳም፤ ሐዋርያትን በአጽናፈ ዓለም፤ መላእክትን
በአጽራርያም እንዳጸናቸው እኛ ሁላችንንም በኦርቶዶክስ
ተዋህዶ እምነታችን በቅድስት ቤተክርስቲያን በበጎ ምግባር
በጾም በጸሎትና በትሩፋት ያጽናን ስለ አባታችን ተክለሀይማኖት
ታሪክ ትንሽ ልበል
አቡነ ተክለ ሃይማኖት ቡልጋ ደብረ ጽላልሽ ወይም ዞረሬ ቅዱስ
ሚካኤል ቤተክርስቲያን የሰበካ ክልል ከአባታቸው ከካህኑ ቅዱስ
ጸጋ ዘአብና ከእናታቸው ቅድስት እግዚእ ኃረያ መጋቢት ፳፬ ቀን
ተፀንሰው፤ በ፲፩፻፺፯ ዓ.ም ታኅሣሥ ፳፬ ቀን ተወለዱ፡፡
በተወለዱ በሦስት ቀናቸው ከእናታቸው እቅፍ ወርደው «አሐዱ
አብ ቅዱስ፣አሐዱ ወልድ ቅዱስ፣ አሐዱ ውእቱ መንፈስ ቅዱስ»
ብለው ሥላሴን አመስግነዋል፡፡ ወላጆቻቸውም ፍስሐ ጽዮን
አሏቸው፡፡ ትርጓሜውም የጽዮን ተድላዋ ደስታዋ ማለት ነው፡፡
በወላጅ አባታቸው በካህኑ ቅዱስ ጸጋ ዘአብ ግብረ ዲቁናን
ሥርዓተ ቤተክርስቲያንን ሲያጠኑ ቆይተው በአሥራ አምስት
ዓመታቸው ከእስክንድርያው ሊቀ ጳጳስ አቡነ ቄርሎስ /
ጌርሎስ/ ዲቁናን ተቀብለዋል፡፡ በዚህም ቅድስት
ቤተክርስቲያንን በወጣትነት ዕድሜያቸው ሲያገለግሉ
ቆይተዋል፡፡
ከዕለታት በአንዱ ቀን ጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖት
ከጓደኞቻቸው ጋር ወደ ዱር አደን ሄደው ሳለ ጌታችን
አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተገልጾ
ለኢትዮጵያውያን ክርስቲያኖች ሐዲስ ሐዋርያ አድርጎ
መረጣቸው። ስማቸውንም «ተክለ ኃሃይማኖት» አለው፡፡
ትርጓሜውም የኃይማኖት ፍሬ ማለት ነው፡፡
አባታችንም ሐዋርያዊ ጉዟቸውን ሲጀምሩ «አቤቱ ጌታዬ
ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ! የመንግሥተ ሰማያትን በር ትከፍትልኝ
ዘንድ እነሆ ቤቴን እንደተከፈተ ተውኩልህ . . . ደካማ ለሆንኩ
ለእኔ ያለ አንተ የሚያፀናኝ የለም። ለምፍገመገም ለእኔ ያለ
አንተ ደጋፊ የለኝም። ለወደቅሁ ለእኔ ያለአንተ የሚያነሳኝ
የለም። ለአዘንኩ ለእኔ ያለአንተ የሚያረጋጋኝ የለም። ለድሀው
ለእኔ ያለ አንተ መጠጊያ የለኝም፡፡» /ገድለ ተክለ ሃይማኖት
ምዕ ፳፰ ቁ ፪ - ፫/
ይህን ብለው ትሕትና በተሞላበትና በተሰበረ ልብ ወደ
ፈጣሪያቸው ከለመኑ በኋላ በልዩ ልዩ የኢትዮጵያ ክፍለ ሀገራት
ከኃጢአት ወደ ገቢረ ጽድቅ፣ ከክህደት ወደ ሃይማኖት
መልሰዋል፡፡ በዚህም የተነሣ ለኢትዮጵያውያን ብርሃን ፀሐይ
ተብለዋል፡፡
ቅዱስ ጳውሎስ በዕብራውያን ክታቡ ስለ ቅዱሳን መንፈሳዊ
ተጋድሎ ሲገልፅ:-
«እነርሱ በእምነት መንግሥታትን ድል ነሱ» /ዕብ. ምዕ ፲፩ ቁ
፴፫ / እንዳለ አባታችን ቅዱስ ተክለ ሃይማኖትም በመንፈሳዊ
ተጋድሎ እንዲሁም በትህትና በተአምራት አላዊ የነበረውን
ንጉሥ ሞቶሎሚን ወደ ክርስትና መልሰዋል፡፡
«ጽድቅን አደረጉ» እንዳለው አባታችን ወንጌልን በተጋድሎ
ሕይወታቸው ተርጉመዋል፡፡
«የአንበሶችን አፍ ዘጉ» ምዕ ፲፩ ቁ ፴፫ /ምዕ ፲፩ ቁ ፴፬ /
እንዳለው አባታችንም የአውሬውን ፥ የዘንዶውን ራስ
ቀጥቅጠዋል።
«ከሰይፍ ስለት አመለጡ» እንዳለው አባታችንም ሞቶሎሚ
ከወረወረው ጦር በተአምራት ድነዋል፡፡
«ከድካማቸው በረቱ» እንዳለው አባታችንም ያለ ዕረፍት በብዙ
ተጋድሎ በጾምና በስግደት በብዙ መከራ በርትተዋል፡፡
ይህን ሁሉ ገድልና ትሩፋት እየፈጸሙ ዕረፍታቸውም በደረሰ ጊዜ
ደቀመዝሙሮቻቸውን «ልጆቼ ሆይ ሁሉም መነኮስ መንግሥተ
ሰማይ ይገባል ማለት አይደለም፤ ዓለምን በሚገባ የናቀ ብቻ
ይገባል እንጂ መጀመሪያ የእግዚአብሔርን ጽድቁን ብቻ ፈልጉ፤
ጾምና ጸሎትን አዘውትሩ፤ እርስ በርሳችሁ ተዋደዱ፤
ትእዛዛቱንም አጥብቃችሁ ጠብቁ እያሉ ይመክሯቸው ነበር. . .»
በኋላም «ለዓለም ጨው ለራሴ አልጫ ሆንኩ፤ ለዓለም
ብርሃን ለራሴ ጨለማ ሆንኩ፣ ከእውነተኛው ዳኛ ከጌታዬ ፊት
ስቆም ምን እመልሳለሁ?» እያሉ በፍጹም ትህትና እና በልዩ
መንፈሳዊ ተመስጦ ይጸልዩ ነበር፡፡
በመጨረሻም አባታችን በነሐሴ ፳፬ ቀን ዕረፍታቸው ሆነ።
በዚህም መሠረት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተክርስቲያናችን
ለእኚህ ዕረፍታቸው በእግዚአብሔር ፊት ለከበረና ብዙ ክብር
ለተሰጣቸው ለጻድቁ ተክለ ሃይማኖት በየዓመቱ በነሐሴ ፳፬
ቀን በዓለ ዕረፍታቸውን በታላቅ ድምቀት ታከብራለች፡፡
እኛንም ከጻድቁ ረድኤት በረከት ይክፈለን፡፡
ሰላም ለዝክረ ስምከ በጥንተ ፊደሉ መስቀል ስም ክቡር
ወስም ልዑል።
ተክለሃማኖት ማቴዎስ በዓለ ቀዳማይ ወንጌል
ከመ እወድሰከ መጠነ አውሥኦተ እክል።
ማዕሠረ ልሳንየ ትፍታሕ ማርያም ድንግል።
ትርጉም ‹‹ የስምህ መነሻ ፊደል የመስቀል ምልክት ለሆነው
እና ክቡር ገናና ለሆነው ስም አጠራርህ ሰላም እላለው ።
የወንጌል ተቀዳሚ ስም ማቴዎስ የተባልክ ተክለሃይማኖት ሆይ
እንደ ችሎታዬ አመሰግንህ ዘንድ አንደበቴ ትፈታልኝ ዘንድ
ድንግል ማርያምን እማልዳለሁ።››
የአባታችን የአቡነ ተክለሃይማኖትን ታሪክ በዘመን እየከፈልን
ባጭሩ ስንመለከተው ደግሞ፡-
የአባታችን የአቡነ ተክለሃይማኖት አባት ቅዱስ ፀጋዘአብ በሸዋ
ቡልጋ ደብረ ጽላልሽ ቅዱስ ሚካኤል ቤተክርስቲያን አገልጋይ
ካህን ነበሩ፡፡ መጋቢት 24 ቀን አባታችን ተክለሃይማኖት
ተፀነሱ በታህሣስ 24 ቀን በ1190 ዓ.ም አባታችን ጻድቁ አቡነ
ተክለሃይማኖት ከእናታቸው ከቅድስት እግዚሐሪያ እና
ከአባታቸው ከቅዱስ ፀጋዘአብ ተወለዱ፡፡ በተወለዱ በ3ኛው ቀን
አሐዱ አብ ቅዱስ፣ አሐዱ ወልድ ቅዱስ፣ አሐዱ ውእቱ መንፈስ
ቅዱስ ብለው ፈጣሪያቸውን አመሠገኑ፡፡ በተወለዱ በ40ኛው
ቀን ክርስትናን በመነሳት ፍስሐ ጽዮን “የጽዮን ደስታ” ተበለው
ተጠሩ፡፡ አባታችን 7 ዓመት እስከሞላቸው ድረስ ከአባታቸው
ከፀጋዘአብ ዘንድ እየተማሩ አደጉ፡፡ አባታችን በ15 ዓመታቸው
ዲቁናን ከጌርሎስ ዘንድ ተቀበሉ፡፡ አባታችን በ22 ዓመታቸው
ከአቡነ ጌርሎስ ዘንድ ቅስናን ተቀበሉ፡፡ በከተታ አውራጃ 3
ዓመት ወንጌልን እያስተማሩ ብዙ ድንቅ ነገርን አደረጉ፡፡
አባታችን በዳዊት ፀሎት ከነቢያት ምስጋና ሌሊቱን ሙሉ ይተጉ
ነበር በያንዳንዱ መዝሙርም 10፣ 10 ስግደትን ይሰግዱ
ነበር፡፡ በሕዳር 24 ቀን ቅዱስ ሚካኤል ወደ ላይ ነጠቃቸው
(አወጣቸው) ከ24ቱ ካህናተ ሰማይ ጋር 25ኛ ካህን ሆነው
የሥላሴን መንበረን “አሐዱ አብ ቅዱስ አሐዱ ወልድ ቅዱስ
አሐዱ ውእቱ መንፈስ ቅዱስ” በማለት አጥነዋል፡፡ በሐይቅ
10 ዓመት በደብረዳሞ 12 ዓመት ኖረዋል፡፡ አባታችን አቡነ
ተክለሃይማኖት በ1267 ዓ.ም ደብረ ሊባኖስን በአት አድርገው
ኖሩ፡፡ ለ22 ዓመት ቆመው በመፀለይ የአንድ እግራቸው አገዳ
ተሠበረ ደቀ መዝሙሮቻቸው በጨርቅ ጠቅልለው ቀበሩት፡፡
በአንድ እግራቸው ለ7 ዓመት በፀሎት ቆሙ በጠቅላላው ለ29
ዓመት በፀሎት ከቆሙ በኋላ በ99 ዓመት ከ10 ወር ከ10 ቀን
ነሐሴ 24 ቀን 1290 ዓ.ም አረፉ አባታችን ባረፉ 54
ዓመታቸው በ1354 ዓ.ም ለአባታችን ለአቡነ እዝቅያስ
ተገልጸው አጽማቸው ከደብረ አስቦ ወደ ደብረ ሊባኖስ ግንቦት
12 ቀን እንዲፈልስ አድርገዋል፡፡
ህዳር 24 ቀን 25ተኛ ካህናተ ሰማይ ሆነው በሠማይ የሥላሴን
መንበር ያጠኑበት
ታህሳስ 24 ቀን የአባታችን ልደት
ጥር 24 ቀን የአባታችን ስባረ አጽም
መጋቢት 24 ቀን የአባታችን ጽንሠት
ግንቦት 12 ቀን የአባታችን ፍልሰተ አጽም
ነሐሴ 24 ቀን የአባታችን እረፍት
የአባታችን ቡራኬ ይድረሰን አሜን!
“ልጆቼ ሆይ ሁሉም መነኩሴ መንግሥተ ሰማይ ይገባል ማለት
አይደለም ዓለምን በሚገባ የናቀ ብቻ ይገባል እንጂ መጀመሪያ
የእግዚአብሔርን ጽድቁን ብቻ ፈልጉ ጾምና ጸሎትን አዘውትሩ
እርስ በእርሳችሁም ተዋደዱ ትዕዛዛቱንም ጠብቁ” የሐዲስ
ኪዳኑ ሙሴ የአባታችን የተክለሃይማኖት ምክር
በደብረ አሚን ከሚገኘው ገድላቸው ደግሞ ባጭሩ፡-
የጻድቅ መታሰቢያ ለበረከት ነው መ ምሳሌ 10፡ 7
የጻድቅ መታሰቢያ ለበረከት ነው እንዳሉ ነቢያት እኛም ነብያትን
ሐዋርያትን ጻድቃንን ሰማእታትን አክብረን ብንቀበላቸው
በረከተ ስጋ በረከተ ነፍስ የምናገኝበት መሆኑንን በማሰብ
ከጻድቃን መካከል አንዱ የሆኑትን የቅዱስ ተክለሃይማኖት ተጋድ
ሎ በትንሹ እንመልከት::አባታችን አቡነ ተክለሃይማኖት ቡልጋ
ደብረ ጽላሎሽ ወይም ዞረሬ ቅዱድ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን
ክልል ከአባታቸው ከጸጋዘአብ ከእናታቸው ከእግዟእኅረያ
ታኅሣሥ 24 ተወለዱ ::በወላጅ አባታቸው በካህኑ ጸጋዘአብ
ግብረ ዲቁናን ስርዓተ ቤተ ክርስቲያንን ሲያጠኑ ቆይተው
ቄርሎስ ከተባሉት ግብጻዊ ጳጳስ በ15 አመታቸው ዲቁናን
ተቀበሉ::እንዲሁም እድሜያቸው 22 አመት ሲሆን ከላይ
ስማቸው ከተገለጹት ጳጳስ የቅስናን ማዕረግ ተቀበሉ ከዚህ
በኋላ ለህዝቡ ወንጌል እየሰበኩ ጣዖት አጋንንትን እያደቀቁ
ህዝቡን አምልኮተ ጣዖት ወደ አምልኮተ እግዚአብሔር
መልሰው አባኢየሱስ ሞዓ ወደ ሚገኙበት ገዳም ሐይቅ
እስጢፋኖስ በቅዱስ ሚካኤል መሪነት ሃይቁን በእግራቸው እንደ
ደረቅ መሬት በመርገጥ ወደ ደሴቱ በመግባት የምንኩስናን
በመቀጠል ከአባ ኢየሱስ ሞዓ እጅም የምንኩስናን ቀሚስ
የንጽህናን ምልክት ተቀብለው ለ12 ዓመታት አቡነ አረጋዊ
ወዳቀኑበት ገዳም ደብረ ዳሞ በመግባት በጊዜው ከነበሩት
አበምኔት ከአባ ዮሐኒ ቆብና አስኬማ ተቀብለው በገድል
በቱሩፋት መንፈሳዊ ተጋድሎዋቸውን ቀጠሉ::ከዚህ ሁሉ በኋላ
በደብረ ሊባኖስ ካለችው ገዳመ አስቦ ዋሻ በመግባት ስምንት
ጦሮችን ሁለቱን በፊት ሁለቱን በኋላ ሁለቱን በቀኝ ሁለቱን
በግራ አስተክለው እጆቻቸውን በትምህርተ መስቀል አምሳል
በመዘርጋት የክርስቶስን ህማምና ሞት ነገረ መስቀሉን
በማሰብ በተመስጦ ሌትና ቀን ያለ ማቋረጥ በጾም በጸሎት
በአርምሞ ተወስነው ሲጋደሉ ከቁመት ብዛት የተነሳ ጥር 24
ቀን የእግራቸው አገዳ ተሰብራለች እግራቸው እስኪሰበር
በጸሎት የቆዩባቸው አመታት 22 ናቸው ::በመአልትና በሌሊት
በትጋትና በቁመት በተጋድሎ ብዛት አንዲት የእግራቸው አገዳ
ስትሰበር ዕድሜያቸው 92 አመት ሆኖ ነበር::ከዚህ በኋላ ለ7
አመታት በአንድ እግራቸው ብቻ በመቆም ያለ ምግብ ሌትም
ቀን ምእንቅልፍ በአይናቸው ሳይዞር እንደ ምሰሶ ጸንተው
በተመስጦ በትጋት ለሰው ዘር ሁሉ ድኅነት ሲለምኑ ኖረዋል
::በመጨረሻም አባታችን በነሐሴ ፳፬ ቀን ዕረፍታቸው ሆነ::
የአባታችን የአቡነ ተክለ ሀይማኖት ምልጃና ጸሎታቸው
ረድዔትና በረከታቸው በኛ በልጆቻቸው ላይ ይደርብን አሜን!
ምንጭ ታምረ ተክለሐይማኖት ዘደብረ አሚን
የእግዚአብሔር፣ቸርነት የድንግል ማርያም አማላጅነት፣
የቅዱሳን መላእክት ተራዳኢነት፣ የጻድቃን፣ የሰማዕታት፣
የቅዱሳን ሐዋርያት፣ የቅዱሳን አበው መነኮሳት፣ የቅዱሳት
አንስት፣ የደናግላንና የቅዱሳን ሁሉ ምልጃና ቃል-ኪዳናቸው
ባለንበት ከሁላችን ጋር
ወስብሐት ለእግዚአብሔር ለዘበቅዱሳኒሁ ይሴባሕ ይእዜኒ
ወዘልፈኒ ወለዓለም ዓለም አሜን፡፡ ወአሜን ለይኩን ለይኩን፡፡

Monday, May 30, 2016

=>+*"+<+>ሰማእቱ ጊዮርጊስ<+>+"*+

ሰማእቱ ጊዮርጊስ
በስመ ሥላሴ
ጊዮርጊስ ማለት ኮከብ፣ ብሩህ፣ ሐረገወይን፣ ፀሐይ ማለት ነው።
ቶማስስ ዘልዳ እንዲለው ሀገሩ ልዳ ነው። አባቱ ዞሮንቶስ
(እንስጣስዮስ) በልዳ መስፍንነት ተሹሞ ይኖር ነበር። እናቱ
ትዎብስታ (አቅሌስያ) ትባላለች። ማርታ ድስያ የሚባሉ እህቶች
ነበሩት።
አስር አመት ሲሆነው አባቱ ሞቶ ሞቶ ሌላ መስፍን ተሾመ።
ደግ ክርስታናዊ ነበርና ወስዶ እያስተማረ አሳደገው። እርሱም
ፈረስ መጋለብ ቀስት መወርወር ለመደ። ጦር ሜዳ ወጥቶ
ከጠላቶቹ መሀል ገብቶ “እኔ የክርስቶስ ወታደር ጊዮርጊስ
መጣሁባችሁ” ሲላቸው ደንግጠው ይሸሹ ነበር።
ጽኑ የእምነት አርበኛ በመኳንንቱ በሹማምንቱ በነገስታቱ ፊት
የማይፈራ ድንቅ ወጣትም ነበር። ሃያ ሲሞላው መስፍኑ የ 15
ዓመት ቆንጆ ልጅ ነበረችውና እሷን ድሮለት ሀብቴን ወርሶ
ይኑር ብሎ ድግስ ሲያስደግስ ዳስ ሲያስጥለ ጌታ ቅዱስ
ጊዮርጊስን ለዚህ አላጨውምና የመስፍኑን ነፍስ ወሰደ።
እርሱም ሀዘኑን ጨርሶ ወደ ቤሩት ሄደ። ቤሩት በኢያርኮ
አቅራቢያ ያለች ሀገር ናት። በዚያ በቤሩት ሰዎች
እግዚአብሔርን የማያውቁ ለዴጎን የተንበረከኩ ናቸው።
ቤሩታዊቷንም የሹም ልጅ ለዚሁ ዘንዶ ግብር ሊገብሩለት
ከግንድ ወስዶ አሰሩለት። ቅዱስ ጊዮርጊስም በዚያ ሲያልፍ
የልጅቱን የጩኸት ድምጽ ሰማ። እሱም ምን ሆነሽ ነው?
አላት። ለደራጎን ተሰጥቼ ነው አለችው። አምላካችሁ ወዴት አለ
አላት ምግቡን ሊፈልግ ሄዷል አለችው። ይህን እያነጋገራት እያለ
ደራጎኑ ምድሪቱን እያነዋወጠ መጣ። ሂድ ይበለሃል ስትለው፤
እኔማ ምን አለኝ ከኔ ጋር ያለው ግን ከሱ ይበልጣል አላት።
ሊበላው ሲቀርብ ስመ እግዚአብሔር ጠርቶ ቢያማትብበት በላዩ
ያደረው ሰይጣን እንደ ጉም ተኖ እንደትቢያ በኖ ጠፋ፤ ሃይሉም
ደከመ። ቤሩታዊቷ አንገቷን በታሰረችበት ገመድ አስሮት እሷ
እየጎተተች እሱ በፈረስ ሆኖ ከተማ ደረሰ። ሕዝቡን ሊያስፈጅ
ነው ብለው ይሸሹ ጀመር። አጽናንቶ መለሳቸው። ንጉሱ
ዱድያኖስ ግን ተነሳስቶበት ክርስቶስን ካድ ባለው ጊዜ አምላኬ
ክርስቶስን አልክድም በማለቱ ተቆጥቶት ጥጋውን በመቃጥን
አስተፍትፎታል፤ ረጅም ችንካሮች ያለበት የብረት ጫማ
አጫምቶታል፤በችንካር አስቸንክሮታል፤ በፈላ ውሃ ውስጥ
አስጨምሮታል።
አጥንቱን አስከስክሶታል። መሄድ እስኪያቅተው ድረስ፤
መርዝም በጥብጦ አጠጥቶታል። በመንኩራኩር አስፈጭቶት
ከጥልቅ ጉድጓድ ጥሎታል። ብዙውን ጊዜ በመንኩራኩር
ተፈጭቷል፤ በኋላም በደብረ ይድራስ ላይ አጥንቱን በትኗል።
መከራ ፈተና አብዝቶበታል። ፯ ጊዜ ሞቶ ፯ ጊዜ ተነስቷል።
አቤት የቅዱሳን መከራቸ፤ ለዚህ እኮ ነው ቅዱስ ጳውሎስ
“እነርሱ በእምነት መንግሥታትን ድል ነሡ፥ ጽድቅን አደረጉ፥
የተሰጠውን የተስፋ ቃል አገኙ፥ የአንበሶችን አፍ ዘጉ፥ የእሳትን
ኃይል አጠፉ፥ ከሰይፍ ስለት አመለጡ፥ ከድካማቸው በረቱ፥
በጦርነት ኃይለኞች ሆኑ፥ የባዕድ ጭፍሮችን አባረሩ። ሴቶች
ሙታናቸውን በትንሣኤ ተቀበሉ፤ ሌሎችም መዳንን ሳይቀበሉ
የሚበልጠውን ትንሣኤ እንዲያገኙ እስከ ሞት ድረስ ተደበደቡ፤
ሌሎችም መዘበቻ በመሆንና በመገረፍ ከዚህም በላይ
በእስራትና በወኅኒ ተፈተኑ፤ በድንጋይ ተወግረው ሞቱ፥ ተፈተኑ፥
በመጋዝ ተሰነጠቁ፥ በሰይፍ ተገድለው ሞቱ፥ ሁሉን እያጡ
መከራን እየተቀበሉ እየተጨነቁ የበግና የፍየል ሌጦ ለብሰው
ዞሩ፤ ዓለም አልተገባቸውምና በምድረ በዳና በተራራ፥ በዋሻና
በምድር ጕድጓድ ተቅበዘበዙ። እነዚህም ሁሉ በእምነታቸው
ተመስክሮላቸው ሳሉ የተሰጠውን የተስፋ ቃል አላገኙም፥ ያለ
እኛ ፍጹማን እንዳይሆኑ እግዚአብሔር ስለ እኛ አንዳች
የሚበልጥ ነገርን አስቀድሞ አይቶ ነበርና። (ዕብ.፲፩፡፴፫-፵)
11፡33-40
ነፍሱን ሊያድን የሚወድ ሁሉ ያጠፋታል፤ ስለ እኔ ግን ነፍሱን
የሚያጠፋ ሁሉ ያገኛታል። ሰው ዓለሙን ሁሉ ቢያተርፍ
ነፍሱንም ቢያጐድል ምን ይጠቅመዋል? ወይስ ሰው ስለ ነፍሱ
ቤዛ ምን ይሰጣል? የሰው ልጅ ከመላእክቱ ጋር በአባቱ ክብር
ይመጣ ዘንድ አለውና፤ ያን ጊዜም ለሁሉ እንደ ሥራው
ያስረክበዋል።(ማቴ.16፡ 25-27
እኔን የሚወድ ቢኖር እራሱን ይካድ መስቀሌንም ተሸክሞ /
መከራዬን ሳይሰለች/ ዕለት ዕለት ይከተለኝ፡፡ ማቴ 10፡38-42
እንዲል ወንጌል
ስለ ጽድቅ የሚራቡና የሚጠሙ፣ እንዲሁም የሚሰደዱ ብጹዓን
ይጠግባሉና፣ መጽናናትንም ያገኛሉና… ጌታ በተራራ ስብከቱ
ከተናገራቸው፣ ካስተማራቸው የሕይወት ምግብ የሆነ ቃሉ
ማቴ.5፡1-ፍጻሜ
ጊዮርጊስ ሆይ ጨካኝ ቁጡ በሆነው በዱድያኖስ አደባባይ ልዩ
ልዩ ተዓምራትህን እንደማድረግህ በጠዋት በማታ በከንቱ ነገር
የሚነሳሱብኝ ጠላቶቼ ሁሉ እንደ አመድ በነው እንደ ጢስ ተነው
ይጥፉ፡፡
ጊዮርጊ ሆይ ሰማዕታት ሁሉ አለቃ እንደመሆንህ ቀድሞ ሰብዓ
ነገስታትን እንደደመሰስካቸው ነበልባላዊ በምትሆን ጸሎትህ
ጠላቶቼን ደምስሳቸው፡፡
ተዓምረኛው ሰማዕት ሆይ ቀድሞ የቢፋሞንን ልጅ ከሰዕበተ
ሃጢአት ሰውነቱን እንድቀደስከው መንግስተ ሰማያትን
ለመውረስ እበቃ ዘንድ ሰውነቴን በፍጹም መቀደስ ከሃጢአት
ርኩሰት ንጹህ አድርግልኝ፡፡
ተዓምረኛው ሰማዕት ሆይ ሙታንን የማስነሳት ሥልጣን
ተሰጥቶሃልና አቤቱ ቤሩታዊትን ከአፈ ዘንዶ እንዳዳንካት እኔን
ከእለተ እኪት ከዘመነ መንሱት በጸሎትህ አድነኝ፡፡
አቤቱ የቅዱስ ጊዮርጊስ አምላክ ሆይ ማረን፤አቤቱ የቅዱስ
ጊዮርጊስ አምላክ ሆይ ራራልን፤ አቤቱ የቅዱስ ጊዮርጊስ
አምላክ ሆይ ይቅር በለን፡
እግዚአብሔር አምላካችን ሰማዕታትን በደም ቅዱሳንን
በገዳም ሐዋርያትን በአጽናፍ ዓለም መላዕክትን በአጽራርያም
እንዳጸናቸው እኛ ሁላችንንም በኦርቶዶክስ ተዋህዶ እምነታችን
በቅድስት ቤተክርስቲያን በበጎ ምግባር በጾም በጸሎትና
በትሩፋት ያጽናን አሜን አሜን አሜን!!!
ወስብሐት ለእግዚአብሔር

Saturday, May 28, 2016

=>+*"+<+>ግንቦት 20-የከበረ አፄ ካሌብ ታሪክ<+>+"*+

አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
አሜን
ግንቦት 20-የከበረ ጻድቅ የኢትዮጵያ ንጉሥ ዐፄ ካሌብ ዕረፍቱ
ነው፡፡ እርሱም የናግራን ሰማዕታትን ደም የተበቀለና በኋላም
ንግሥናውን ትቶ ዓለምን ንቆ በመመንኮስ ዋሻ የገባ ነው፡፡
የነገሠበትን የወርቅ ዘውዱንም በጌታችን መቃብር ላይ
አስቀምጡልኝ ብሎ ለኢየሩሳሌሙ ሊቀ ጳጳስ ለአባ ዮሐንስ
ልኮለታል፡፡
+ ከአባቶች መምህራን 16ኛ የሆነ በደብረ ሊባኖስ አበ ምኔት
ሆኖ ያገለገለ የከበረ አባ በትረ ወንጌል ዕረፍቱ መሆኑን
ስንክሳሩ በስም ይጠቅሰዋል፡፡
+ ዳግመኛም በዚኽች ዕለት የሀገረ ቶናው የከበረ አባ አሞንዮስ
ዕረፍቱ ነው፡፡
+ የቅዱስ አሞኒ ረድእ የሆነው አባ ዳርማ ዕረፍቱ መሆኑን
ስንክሳሩ በስም ይጠቅሰዋል፡፡
ጻድቁ ንጉሥ ዐፄ ካሌብ፡- ይኽም ጻድቅ ንጉሥ የናግራን
ሰማዕታትን ደም የተበቀለና በኋላም ንግሥናውን ትቶ ዓለምን
ንቆ በመመንኮስ ዋሻ የገባ ነው፡፡ የነገሠበትን የወርቅ
ዘውዱንም በጌታችን መቃብር ላይ አስቀምጡልኝ ብሎ
ለኢየሩሳሌሙ ሊቀ ጳጳስ ለአባ ዮሐንስ የላከ ነው፡፡ ስለ
እርሱም መጽሐፈ ስንክሳሩ ላይ እና አቡነ አረጋዊ ገድል ላይ
የተጻፈውን እያነበብን ዛሬ በሃገራችን ከሚከበረው ብሔራዊ
በዓል ጋር እናነጻጽረው እስቲ! (ምንም እንኳን ብርሃንና
ጨለማ ለንጽጽር ባይበቁም)
ከመጽሐፈ ስንክሳር፡- በቍስጥንጥንያ ዮስጢኖስ በነገሠ
በ5ኛው ዓመት ዐፄ ካሌብ በኢትዮጵያ ነግሦ ነበር፡፡ የአይሁድም
ንጉሥ ፊንሐስ ነበር፡፡ በዚህም ወቅት ሊቃነ ጳጳሳት የነበሩት
የኢየሩሳሌሙ አባ ዮሐንስ፣ የቍስጥንጥንያው አባ ጢሞቴዎስ፣
የእስክንድርያውም አባ ጢሞቴዎስ፣ የአንጾኪያው አባ
አውፍራስዮስ ነበሩ፡፡ ሳባ የምትባለው አገር በኢትዮጵያ
ነገሥታት እጅ ውስጥ ነበረች፡፡
የሮም ነገሥታት አስባስያኖስና ጥጦስ አይሁድን ወረው
ከኢየሩሳሌም አሳደዷቸውና ይህችን ሳባን አይሁድ ወረሷት፡፡
በውስጧም በጌታችን የሚያምኑ ብዙ ሕዝቦች ነበሩባት፡፡ በሳባ
ውስጥም ክርስቲያኖች የሚኖሩባት ታላቅ ከተማ ነበረች፡፡
የአይሁድ ንጉሥ ፊንሐስም ወደ ከተማዋ ገብቶ በሺህ
የሚቆጠሩትን ክርስቲያኖች ገደለ፡፡ ዙሪያ ዳር ድንበሯ
በመስቀል ምልክት የታጠረች ስለነበረች ፊንሐስ መጀመሪያ
መግባት ሳይችል ቢቀር ‹‹ወደ ውስጥ ገብቼ የከተማዋን
አሠራር፣ ገበያዋን፣ አደባባዮቿን መጎብኝት እሻለሁ እንጂ ክፉ
አላስብም፣ የማንንም ደም አላፈስም›› ብሎ ከነሠራዊቱ ከገባ
በኋላ ግን መግደል ጀመረ፡፡ መጀመሪያውንም አቡነ ኂሩተ
አምላክ ‹‹ውሸቱን ነው አታስገቡት፣ ሐሰተኛ ነው ደጁን
ከፍታችሁ አታስገቡት›› ብለው ቢነግሯቸውም የሚሰማቸው
ጠፋ፡፡ ፊንሐስም እንደገባ የሕዝቡን ገንዘብ ዘረፈ፤ ቀጥሎም
ነበልባሉ አየር ላይ ደርሶ እስኪታይ ድረስ እሳት አስነድዶ
‹‹ኤጲስ ቆጶሱን አባ ጳውሎስን አምጡልኝ›› ብሎ አዘዘ፡፡
እንደሞቱም ሲነገረው ዐፅማቸውን ከመቃብር አውጥቶ
አቃጠለው፤ ቀጥሎም ቀሳውስትን፣ ካህናትን፣ ዲያቆናትን፣
መነኮሳትን ሁሉ በእሳቱ ውስጥ እንዲጨምሯቸው አዘዘ፡፡
አራት ሺህ ሃያ ሰባት ክርስቲያኖችም ወደ እሳቱ ተጥለው
በሰማዕትነት ሞቱ፡፡
ፊንሐስም አቡነ ኂሩተ አምላክንና ታላላቅ መኳንንትን ግን
አሳስሮ ብዙ አሠቃያቸው፡፡ ‹‹ክርስቶስን ያልካደ ሁሉ ተሠቃይቶ
ይሞታል›› የሚል አዋጅ በከተማው እንዲነገር አዘዘ፡፡ አቡነ
ኂሩተ አምላክንም አስሮ እያሠቃያቸው በከተማው አዞራቸው፡፡
ሕዝቡም ‹‹ጌታችንን አንክድም›› እያሉ ወጥተው ተገደሉ፡፡
በዚህም ጊዜ የተገደሉት ቁጥራቸው 4252 ሆነ፡፡ የአቡነ አቡነ
ኂሩተ አምላክን ሚስት ቅድስት ድማህን ከ2 ልጆቿ ጋር ይዞ
አሠቃያቸው፡፡ አንደኛዋም የ12 ዓመት ሕፃን ምራቋን
በፊንሐስ ላይ ተፋችበት፣ እርሱም ሰይፉን መዞ አንገቷን
ቆረጠው፡፡ ለእናቷ ለቅድስት ድማህም የልጇን ደም አጠጣት፡፡
ድማህም ‹‹ይህን እንዲሆን የፈቀደ እግዚአብሔር ይክበር
ይመስገን›› ብላ አምላኳን ስታመሰግን ሰምቷት በንዴት
እናቲቱንም አንገቷን ቆረጠው፡፡
ፊንሐስም አቡነ ኂሩተ አምላክን ግን ወደ ውጭ አውጥቶ
‹‹የምታመልኩትን ክርስቶስን ካዱ›› አላቸው፡፡ አቡነ ኂሩተ
አምላክም ‹‹ክብር ይባውና ጌታዬን ኢየሱስ ክርስቶስን
እያለመኩ ስኖር 78 ዓመት ሆነኝ፣ እስከ አራት ትውልድም
ለማየት ደርሻለሁ፡፡ ዛሬም ስለከበረ ስሙ ምስክር ሆኜ ስሞት
እጅግ ደስ ይለኛል፡፡ ወደዚህ ለመግባት ስትምል እኔም
አስቀድሜ መሐላህን እንዳያምኑ ለወገኖቼ ነግሬአቸው ነበር፤
አንተ ሐሰተኛ ነህና ነገር ግን ይህ ሁሉ የእግዚአብሔር ፈቃድ
ነው፤ ለዚህ ተጋድሎ ላበቃኝ ለእርሱ ምስጋና ይሁን›› እያሉ
ፊንሐስን በተናገሩት ጊዜ ወደ ወንዝ ወስዶ አንገታቸውን
አስቆረጠው፡፡ አቡነ ኂሩተ አምላክ በሰማዕትነት ከማረፋቸው
በፊት የኢትዮጵያንና የሮምን መንግሥት ያጸና ዘንድ የአይሁድን
መንግሥት ግን ያጠፋ ዘንድ ጌታችንን ለመኑት፡፡ ዕረፍታቸውም
ኅዳር 26 ቀን ነው፡፡ አቡነ ኂሩተ አምላክም ሕዝቡን
ተሰናብተው በተሰየፉ ጊዜ አንዲት ሴት ደማቸውን ለ5 ዓመቱ
ልጇ ቀባችው፡፡
ይህንንም ሲያዩ ልጇን ነጥቀው ለንጉሡ ሰጥተው እርሷን
ከእሳቱ ውስጥ ጨመሯት፡፡ ንጉሡ ፊንሐስም ሕፃኑን ‹‹እኔን
ትወዳለህ ወይስ ክርስቶስ የሚሉትን?›› ብሎ ጠየቀው፡፡ የ5
ዓመቱ ሕፃንም ‹‹እኔስ የእጁ ሥራ ነኝና ክርስቶስን እወደዋለሁ፣
ይልቅስ ልቀቀኝና ወደ እናቴ ልሂድና ሰማዕትነቴን ልፈጽም››
አለው፡፡ ፊንሐስም ከእጁ እንዳይወጣ በያዘው ጊዜ እግሩን
ነክሶት አምልጦት ሮጦ ሄዶ ከእሳቱ ውስጥ ገባ፡፡ ሁለተኛም
የ10 ወር ሕፃን የተሸከመች አንዲት አማኝ ሴት ወደ ልጇ
እያየች ‹‹ልጄ ሆይ ዛሬስ ላዝንልህ አልቻልኩም›› ብላ ስትናገር
በእቅፏ ያለው የ10 ወሩ ሕፃን ልጇም አንደበቱን ከፍቶ ‹‹እናቴ
ሆይ በፍጥነት ወደ ዘላለም ሕይወት እንሂድ ይህችን እሳት ከዛሬ
በቀር አናያትምና›› አላት፡፡ እርሷም ልጇን ይዛ ዘላ እሳቱ
ውስጥ ተወርውራ ገባች፡፡ የክርስቲያን ወገኖችም ይህን ሁሉ
አይተው እኩሉ ወደ እሳት እኩሉ ወደ ሰይፍ ተሽቀዳደሙ፡፡
ራሳቸው የአይሁድ ሠራዊት ዕፁብ ብለው እስኪያደንቁ ድረስ
ክርስቲያኖቹ ወደ ሰማዕትነት ተፋጠኑ፡፡ በዚህም ጊዜ የሞቱት
ቁጥራቸው ሃያ ሺህ ነበር፡፡ ክርስቲያኖቹም በሞሞቱበት ጊዜ
የረዳቶቻቸውን የቊስጥንጥንያንና የኢትዮጵያን ነገሥታት ስም
በጸሎታቸው ይጠሩ ነበር፡፡ ከዚህም በኋላ እሳቱ በሰማይ ውስጥ
መልቶ 40 ቀንና 40 ሌሊት ታየ፡፡
ፊንሐስም ወደ ሀገሩ በተመለሰ ጊዜ ወደ ነገሥታቱ ሁሉ በኋይሉ
እየተመካ ላከባቸው፡፡ የሮሜው ንጉሥ ዮስጢኖስም ይህን
ሰምቶ ወደ እስክንድርያ ሊቀ ጳጳስ ወደ አባ ጢሞቴዎስ
መልአክት ላከ፡፡ ለሀገረ ናግራን ክርስቲያኖች ደማቸውን
ይበቀልላቸው ዘንድ ለኢትዮጵያው ንጉሥ ለዐፄ ካሌብ
መልእክት እንዲልክ ነገረው፡፡ ዐፄ ካሌብም መልእክቱ
ሲደርሰው ፈጥኖ ተነሣና በዋሻ ከሚኖር ከአቡነ ጰንጠሌዎን
በረከትን ተቀብሎ ለአቡነ አረጋዊም በጸሎት እንዲያስቡት
ደብዳቤ ጽፎ ከላከ በኋላ ከሠራዊቱ ጋር በመርከብ ተጭኖ ወደ
ሀገረ ናግራን ሄደ፡፡ ከመሄዱም በፊት ለአቡነ አረጋዊ የላከላቸው
መልእክት እንዲህ የሚል ነው፡- ‹‹ፊንሐስ የተባለ አረማዊ
የናግራን ክርስቲያኖችን ደም በከንቱ ያፈሰሰ፣ ቤተ ክርስቲያንን
የመዘበረና ያጠፋ ፍጹም የእግዚአብሔር ጠላት ወደሚሆን ሄጄ
እዋጋው ዘንድ ተዘጋጅቻለሁ፡፡ ስለዚህ አባቴ ሆይ! አንተም
በበኩልህ ጸሎት አድርግልኝ፣ የጻድቅ ጸሎት ትራዳለች፣
ኃይልንም ታሰጣለች፣ በጠላት ላይ ድልንም ታቀዳጃለችና››
ሲል ላከበት፡፡ አባታችን አቡነ አረጋዊም ለንጉሡ ጭፍሮች
‹ወደ ጦሩ ግንባር ሂድ፣ እግዚአብሔር ጠላቶችህን ከእግርህ
በታች ያስገዛልህ፣ ለአንተም ግርማ ሞገስ ይስጥህ፣ በሰላም
ይመልስህ›› ብለው መርቀው ላኩለት፡፡ ከዚህ በኋላ ዐፄ ካሌብ
ልብሰ መንግሥቱን አውልቆ ጥሎ ማቅ ለብሶ በፍጹም ልመና
ብዙ ጸሎት አደረገ፡፡
ከዚህም በኋላ ዐፄ ካሌብ ሰባ ሺህ ጦሩን አዘጋጅቶ ወደ የመን
ሳባ በመርከብ ተጓዘና ከከሐዲው ፊንሐስ ጋር ጦር ገጠመ፡፡
ከሐዲውን ንጉሥ ፊንሐስን ራሱ ዐፄ ካሌብ ገጠመውና በፈረሱ
ላይ እንደተቀመጠ በጨበጣ በጦር ወግቶ ገደለውና ወደ ባሕር
ገልብጦ ጣለው፡፡ ከዚያም ዐፄ ካሌብ ዛፋር ወደምትባለው
ከተማ ሄዶ እርሷንም ተቆጣጠራት፡፡ በእዚያም ያሉ የፊንሐስን
ሹማምንቶች እያፈላለገ በአደባባይ እንዲገደሉ በማድረግ
የክርስቲያኖቹን ደም በሚገባ ተበቀለ፡፡ የናግራንንም
ሕንፃዎዋን አደሰ፤ የሰማዕታቱንም መታሰቢያ አቆመ፡፡ ወደ
እስክንድርያው አባ ጢሞቴዎስና ወደ ሮሜው ንጉሥ
ዮስጢኖስም የድል መልእክት ላከላቸውና እነርሱም ሰምተው
እጅግ ተደሰቱ፡፡ በአንጾኪያ፣ በእስክንድሪያ፣ በሮም፣
በቊስጥንጥንያና በዓለም ላይ ያሉ ክርስቲያኖች ሁሉ ይህን
ሲሰሙ በእጅጉ ተደሰቱ፡፡ ይህም የሆነው በ525 ዓ.ም ነው፡፡
ጠፍተው የሄዱ ክርስቲያኖችንም ሰበሰባቸውና ወደቀደመ
ቦታቸው መለሳቸው፣ ቤተክርስቲያናቸውን አነጸላቸው፡፡ ከሳባ
ሀገር የማረከውን ንብረት ሁሉ ለቤተክርስቲያን ሰጥቶ ዓሥር
ሺህ ጠባቂ ሠራዊት ሰቷቸው ወደ አክሱም በሰላምና በፍጹም
ደስታ ተመለሰ፡፡
ከአቡነ አረጋዊ ገድል፡- በቍስጥንጥንያ ዮስጢኖስ በነገሠ
በ5ኛው ዓመት ዐፄ ካሌብ በኢትዮጵያ ነግሦ ነበር፡፡ የአይሁድም
ንጉሥ ፊንሐስ ነበር፡፡ በዚህም ወቅት ሊቃነ ጳጳሳት የነበሩት
የኢየሩሳሌሙ አባ ዮሐንስ፣ የቍስጥንጥንያው አባ ጢሞቴዎስ፣
የእስክንድርያውም አባ ጢሞቴዎስ፣ የአንጾኪያው አባ
አውፍራስዮስ ነበሩ፡፡ ‹‹ከክርስቶስ ልደት 524 ዓመት በኋላ
በናግራን ሀገር በክርስቲያኖች በአይሁዶችና በአረማውያን
መካከል ከባድ ፀብ ተነሣ፡፡ ማዝሩቅ ወይም ፊንሐስ የተባለው
የሂማሪያው ንጉሥ የአይሁዶችንና የአረመኔዎቹን ምክር
እየተቀበለ ክርስቲያኖቹን ፈጃቸው፣ አብያተ ክርስቲያናቱንም
ሁሉ አቃጠለ፡፡ አረማዊው ንጉሥ ‹አምላካችሁን ክርስቶስን
ብትክዱት ሕይወታችሁ ይጠበቃል› ቢላቸውም ክርስቲያኖቹ ግን
‹ስለ አምላካችን ስለ ክርስቶስ መሞትን አንፈራም› ስላሉትና
በእምነታቸው ስለጸኑ የክርስቲያኖቹ መሪ የ95 ዓመት ዕድሜ
ያለውን ቅዱስ ኂሩት ከነቤተሰቦቹ በመጀመሪያ በንጉሡ ፊት
ለፍርድ ቀረበ፡፡ ለንጉሡም በድፍረት ‹እንዳንተ ባለው ከሐዲ
ንጉሥ ፊት አምላኬን አልክድም› ብሎ ስለመለሰለት ንጉሡም
በንዴት አንገቱ እንዲቆረጥ ፈረደበትና ቅዱስ ኂሩት ከቤተሰቦቹ
ጋር የሰማዕትነትን ክብር ተቀዳጀ፡፡
ቁጥራቸው ብዙ የሆኑ የቅዱስ ኂሩት ተከታዮችንና
ክርስቲያኖችንም ጥልቅ ጉድጓድ ቆፍሮ በዚያ ውስጥ በእሳት
ተቃጥለው እንዲሞቱ አደረጋቸው፡፡ ክርስቲያኖቹም
በሞሞቱበት ጊዜ የረዳቶቻቸውን የቊስጥንጥንያንና
የኢትዮጵያን ነገሥታት ስም በጸሎታቸው እየጠሩ በሰማዕትነት
ሞቱ፡፡ ቁጥራቸው ሃያ ሺህ ነበር፡፡ ይኽ ጨካኝ አረመኔ ንጉሥ
ቀደም ብለው ያረፉትን የኤጲስ ቆጶሱን የጳውሎስን አፅም
አውጥቶ በእሳት አቃጠለው፡፡ እንዲሁም የቀሩትን ክርስቲያኖች
ካሉበት እያደነ በሰይፍና በእሳት አጠፋቸው፡፡ ከጥቂት ጊዜ በኋላ
የቊስጥንጥንያው ሊቀ ጳጳስ ጢሞቴዎስ በናግራን አገር
ስለተፈጁት የክርስቲያን ወገኖች በግፍ የተጨፈጨፉበትን
መልእክት የያዘች ደብዳቤ ወደ ኢትዮጵያው ንጉሥ ወደ ዐፄ
ካሌብ ላከ፡፡ ዐፄ ካሌብም መልእክቱን ከተረዳ በኋላ ወደ ብፁዕ
አቡነ አረጋዊ እንዲህ ሲል መልእክት ላከ፣ ‹ፊንሐስ የተባለ
አረማዊ የናግራን ክርስቲያኖችን ደም በከንቱ ያፈሰሰ፣
ቤተክርስቲያንን የመዘበረና ያጠፋ ፍጹም የእግዚአብሔር ጠላት
ወደሚሆን ሄጄ እዋጋው ዘንድ ተዘጋጅቻለሁ፡፡ ስለዚህ አባቴ
ሆይ! አንተም በበኩልህ ጸሎት አድርግልኝ፣ የጻዲቅ ጸሎት
ትራዳለች፣ ኃይልንም ታሰጣለች፣ በጠላት ላይ ድልንም
ታቀዳጃለችና› ሲል ላከበት፡፡ አባታችን አቡነ አረጋዊም ለንጉሡ
ጭፍሮች ‹ወደ ጦሩ ግንባር ሂድ፣ እግዚአብሔር ጠላቶችህን
ከእግርህ በታች ያስገዛልህ፣ ለአንተም ግርማ ሞገስ ይስጥህ፣
በሰላም ይመልስህ› ብለው መርቀው ላኩበት፡፡ ከዚህ በኋላ ዐፄ
ካሌብ ልብሰ መንግሥቱን አውልቆ ጥሎ ማቅ ለብሶ በፍጹም
ልመና ብዙ ጸሎትን አደረገ፡፡
ዐፄ ካሌብ ታላቅ ጻዲቅ ንጉሥ ነበር፣ ከምድር ነገሥታት ወገን
በመንግሥቱ ዙፋን ላይ ተቀምጦ እያለ እንደ እርሱ ድንቅ
ተአምራት ያደረገ የለም፡፡ ከሁሉ በፊት የዑር አገር ሰዎች
ባመፁበት ጊዜ የሀገሪቱ ሰዎች የጦሩን መትመምና ግስጋሴ
አይተው እንዳይሸሹና እንዳያመልጡ እግዚአብሔር በምድር
ውስጥ መንገድን ከፈተለት፡፡ የመንገዱም ርዝመት በፈጣን ሰው
ሩጫ ሦስት ቀን ያስኬዳል፡፡ ንጉሡ እግዚአብሔር በከፈተለት
የምድር ውስጥ መንገድ ገብቶ ገስግሶ ድንገት ደረሰና
ደመሰሳቸው፣ አጠፋቸውም፡፡ ከእነርሱ አንድ ስንኳ አላስቀረም፣
ሀገሪቱንም በእጁ አገባት፣ እስከዛሬም ድረስ አለች፡፡ ከዚያም
ከ524 ዓ.ም በኋላ ሰባ ሺህ ጦሩን አዘጋጅቶ ቀድሞ ወዳሰበበት
ወደ የመን ሳባ በመርከብ ተጓዘና ከከሐዲው ፊንሐስ ጋር ጦር
ገጠመ፡፡ ከሐዲውን ንጉሥ ፊንሐስን ራሱ ዐፄ ካሌብ ገጠመውና
በፈረሱ ላይ እንደተቀመጠ በጨበጣ በጦር ወግቶ ገደለውና ወደ
ባሕር ገልብጦ ጣለው፡፡ ከዚያም ዐፄ ካሌብ ዛፋር
ወደምትባለው ከተማ ሄዶ እርሷንም ተቆጣጠራት፡፡ በእዚያም
ያሉ የፊንሐስን ሹማምንቶች እያፈላለገ በአደባባይ እንዲገደሉ
በማድረግ የክርስቲያኖቹን ደም በሚገባ ተበቀለ፡፡ በአንጾኪያ፣
በእስክንድሪያ፣ በሮም፣ በቊስጥንጥንያና በዓለም ላይ ያሉ
ክርስቲያኖች ሁሉ ይህን ሲሰሙ በእጅጉ ተደሰቱ፡፡ ይህም
የሆነው በ525 ዓ.ም ነው፡፡ ጠፍተው የሄዱ ክርስቲያኖችንም
ሰበሰባቸውና ወደቀደመ ቦታቸው መለሳቸው፣
ቤተክርስቲያናቸውን አነጸላቸው፡፡ ከሳባ ሀገር የማረከውን
ንብረት ሁሉ ለቤተክርስቲያን ሰጥቶ ዓሥር ሺህ ጠባቂ ሠራዊት
ሰቷቸው ወደ አክሱም በሰላምና በፍጹም ደስታ ተመለሰ፡፡ ከዚህ
በኋላ ዐፄ ካሌብ ‹ይህን ያደረገልኝን አምላኬን በምን
ላስደስተው?› ሲል አሰበና ዓለምን ንቆ፣ መንግሥቱንና ክብሩን
ትቶ መንኩሶ በዋሻ ለመቀመጥ ወሰነ፡፡››
ዐፄ ካሌብ ዓለምን ንቆ፣ ልብሰ መንግሥቱን አውልቆ
በመመንኮስ ዋሻ እንደገባ፡- ‹‹ንጉሡ ዐፄ ካሌብ የናግራን
ሰማዕታት ደም ተበቅሎላቸው ሁሉንም ነገር አስተካክሎላቸው
በደስታ ወደ አክሱም ከተመለሰ በኋላ ‹ይህን ያደረገልኝን
አምላኬን በምን ላስደስተው?› ሲል አሰበና ተድላውን፣
ደስታውን ዓለምን ንቆ፣ ልብሰ መንግሥቱን አውልቆ አንዲት
የውኃ መንቀልና አንዲት ምንጣፍ ብቻ ይዞ አባ ጰንጠሌዎን
ገዳም አጠገብ ከሚገኝ ዋሻ ውስጥ ገብቶ በአባ ጰንጠሌዎን እጅ
መንኩሶ ለመቀመጥ ወሰነ፡፡ አባ ጰንጠሌዎንንም
‹አመንኩሰኝ› አለውና የመላእክትን አስኬማ አልብሶ
አመነኮሰው፡፡ ዳግመኛም ከዋሻው ወጥቶ ዓለምን በዓይኑ
እንዳያይ ማለ፡፡ ዋጋው እጅግ የከበረውንና በነገሠ ጊዜ
የጫነውን ዘውዱን ከጌታችን መካነ መቃብር ወይም በር ላይ
ይሰቀልለት ዘንድ ከአደራ ደብዳቤ ጋር ለኢየሩሳሌሙ ሊቀ
ጳጳሳት ለአባ ዮሐንስ ላከለት፡፡
ዳግመኛም ንጉሡ ዐፄ ካሌብ ‹አባቴ ሆይ በአንተ ጸሎት
በእግዚአብሔር ቸርነት ከጦርነቱ በሰላም ተመልሻለሁ፣
አሁንም የክርስቶስን አርዑተ መስቀል ተሸክሜአለሁና
እግዚአብሔር ለፍጻሜው ያብቃህ እያልህ ስለ እኔ ጸልይልኝ›
ብሎ ወደ አባታቸን ወደ አቡነ አረጋዊ ላከበት፡፡ ስለዚህም ነገር
አባታቸን ወደ አቡነ አረጋዊ በጣም ተደሰቶ ‹ልጄ ሆይ!
መልካሙንና የበለጠውን አድርገሃል፣ አሁንም እግዚአብሔር
የፈቀደከውን ነገር ሁሉ ይፈጽምልህ› ብለው መረቁት፡፡
ኢትዮጵያዊው ንጉሥ ዐፄ ካሌብ ይህን ዓለም በመናቅ በበረሃ
በዋሻ 12 ዓመት በጾም በጸሎት በብዙ ተጋድሎ ሲኖር ቆይቶ
በግንቦት 20 ቀን ዐርፎ እስከ ዘለዓለሙ ድረስ የማያልፍ
ሰማያዊ ክብርን ወረሰ፡፡›› ረድኤት በረከቱ ይደርብን፣ በጸሎቱ
ይማረን፡፡

Friday, May 27, 2016

=>+*"+<+>#መልዐኩ_ቅዱስ_ገብርኤል<+>+"*+

“የእግዚአብሔር መልአክ በሚፈሩት ሰዎች ዙሪያ ይሰፍራል፥
ያድናቸውማል።” መዝ. 33፡7፡፡ ይህ ጥቅስ የእግዚአብሔር
መልአክ እግዚአብሔርን የሚፈሩትን ሰዎች ከእግዚአብሔር
ተልኮ በዙሪያቸው ሆኖ ከመከራ እንደሚያድናቸው
ያስተምራል፡፡ የመላእክት አንዱ ተግባር መዳንን ይወርሱ ዘንድ
ያላቸውን ሰዎች መጠበቅ መሆኑ ተጽፏል፡፡ “ሁሉ መዳንን
ይወርሱ ዘንድ ስላላቸው ለማገዝ የሚላኩ የሚያገለግሉም
መናፍስት አይደሉምን?” ዕብ. 1፡14፡፡
ከጠላት ከሚመጣ መከራ የሚታደግ መልአክ
ቅዱስ ገብርኤል ቅዱሳን ይሆኑ ዘንድ ለተጠሩት መንፈሳዊ
እውቀቱን የሚያካፍላቸው መልአክ ብቻ አይደለም፤
ለእግዚአብሔር በመገዛታቸው ምክንያት ከአላውያን ገዢዎች
ከሚደርስባቸው መከራም የሚታደጋቸው መልአክም ነው፡፡
የፋርስ ንጉሥ የነበረው ናብከደነፆር እግዚአብሔር አምላክ
ምድሪቱን ሁሉ ሲያስገዛለት በትዕቢት ተሞልቶ “በኃይሌ
አደርጋለሁ፣ በማስተዋል ጥበቤም የአሕዛብን ድንበሮች
አርቃለሁ፣ ሀብታቸውንም እዘርፋለሁ፣ የሚቀመጡባቸውንም
ከተሞች አናውጣለሁ፣ በእጄም ዓለምን ሁሉ እንደ ወፍ ቤት
እሰበስባለሁ፣ እንደ ተተወ እንቁላልም አወስዳቸዋለሁ፤ከእኔም
የሚያመልጥ የለም የሚቃወመኝም የለም፡፡”(ኢሳ.10፡13
-14) ብሎ በመታበይ የወርቅ ጣዖትን አሠርቶ ዱራ(አዱራን)
በሚባል ስፍራ ላይ አቆመው፡፡ በግዛቱ በልዩ ልዩ የሥልጣን
እርከን ላይ ያሉትን ሹማምንቱንና ገዢዎችን ሰበሰባቸው፤
“የመለከትና የእንቢልታ የመሰንቆና የክራር የበገናና የዋሽንትን
የዘፈንንም ሁሉ ድምፅ በሰማችሁ ጊዜ ወድቃችሁ ንጉሥ
ናብከደነፆር ላቆመው ለወርቁ ምስል ስገዱ፡፡ ወድቆም
ለማይሰግድ በዚያን ጊዜ በሚነድድ እሳት እቶን ውስጥ ይጣል”
ብሎ አዋጅ አስነገረ፡፡ ይህን አዋጅ የሰሙ የንጉሥ ሹማምንት
ሁሉ የመለከቱና የእንቢልታው እንዲህም የዘፈን ድምፅ በተሰማ
ጊዜ ተደፍተው ለወርቁ ምስል ሰገዱ፡፡ በባቢሎን አውራጃዎች
ላይ የተሾሙ አዛርያ(ሲድራቅ)፣ አናንያና(ሚሳቅ) ሚሳኤል
(አብደናጎ) ግን ንጉሥ ላቆመው ምስል አልሰገዱም፡፡ ነገር
ሠሪዎችም ይህንን ወሬ ለንጉሥ ነገሩት፤ ንጉሥም እጅግ
ተቆጥቶ ወደ እርሱ አስጠራቸው፡፡ እርሱ ላቆመው ለወርቅ
ምስል ያልሰገዱ እንደሆነ እጅና እግራቸውን ታስረው ወደ እቶን
እሳቱ እንደሚጣሉ አስጠነቀቃቸው፡፡ ሠልስቱ ደቂቅ ግን
“ናብከደነፆር ሆይ! በዚህ ነገር እንመልስልህ ዘንድ
አንፈልግም፡፡ ንጉሥ ሆይ! እኛ የምናመልከው አምላክ በሰማይ
አለ፣ ከሚነደውም ከእሳቱ እቶን ያድነን ዘንድ ይችላል፤
ከእጅህም ያድነናል፤ ንጉሥ ሆይ! ይህም ባይሆን አማልክትህን
አንዳናመልክ፣ ላቆምኸውም ለወርቁ ምስል እንዳንሰግድለት
እወቅ” ብለው መለሱለት፡፡ የንጉሥ ናብከደነፆር ቁጣ ከፊት
ይልቅ እጅግ ነደደ እሳቱንም ሰባት እጥፍ እንዲያቀጣጥሉና
እነዚህን ሦስት ብላቴኖች እጅና እግራቸውን አስረው ከእነ
ማዕረገ ልብሳቸው ከእቶን እሳት ውስጥ እንዲጨምሩአቸው
ትእዛዝን አስተላለፈ፡፡ ትእዛዙ አስቸኳይ ነበርና ወደ እሳት
ጣሏቸው: ወደ እሳቱ የጣሏቸውም ኃያላን በእሳቱ ወላፈን
ተገርፈው ሞቱ፡፡ እንዲህ ሲሆን ሳለ ግን ሠልስቱ ደቂቅ ወደ
አምላካቸው “በፍጹም ልባችን እናምንሃለን፣ እንፈራሃለን፣
አታሳፍረን እንጂ ገጸ ረድኤትህንም እንፈልጋለን፡፡” እያሉ
ይጸልዩ ነበር፡፡ እግዚአብሔር አምላክ ጸሎታቸውን ተቀበለ፤
መልአኩ ቅዱስ ገብርኤልንም ከመጣባቸው መከራ ይታደጋቸው
ዘንድ ላከው፡፡ ቅዱስ ገብርኤልም እስራታቸውን ፈታ፤ እሳቱን
እንደ ውኃ አቀዘቀዘው፡፡
ሠልስቱ ደቂቅም መልአኩን ልኮ ከዚህ እቶን እሳት ያዳናቸውን
አምላክ “የአባቶቻችን አምላክ እግዚአብሔር ይክበር:
ስምህም ለዘለዓለም የተመሰገነና የከበረ ነው” በማለት
አመሰገኑት፡፡ ንጉሥ ናብከደነፆርም ሠልስቱ ደቂቅ እሳቱ
አንዳች ጉዳት ሳያደርስባቸው በእሳት ውስጥ ሲመላለሱ ከእነርሱ
ጋር የሰው መልክ ያለው ነገር ግን የአምላክን ልጅ የሚመስል
መልአክ ተመለከተ፡፡ መንፈስ ቅዱስ ሊቀ ካህናቱን ቀያፋን
ፊቱን ጸፍቶ አፉን ከፍቶ “ሕዝቡ ሁሉ ከሚጠፋ አንድ ሰው
ስለሕዝቡ ይሞት ዘንድ እንዲሻለን አታስቡምን”(ዮሐ.11፡4
9) ብሎ እንዳናገረው እንዲሁ ናብከደነፆርንም “እነሆ እኔ
የተፈቱ በእሳቱም መካከል የሚመላለሱ አራት ሰዎችን በዚያ
አያለሁ ምንም የነካቸው የለም፤የአራተኛውም መልክ
የእግዚአብሔርን ልጅ ይመስላል” ብሎ እንዲናገር አደረገው፡፡
የእግዚአብሔር ልጅን መልክ ያለው: በኋላም መልአክ ብሎ
የተናገረለት ቅዱስ ገብርኤልን ነበር፡፡
እርሱ ስለመሆኑ ለነቢዩ ዳንኤል በተገለጠበት ግርማ ማረጋገጥ
እንችላለን፡፡ ናብከደነፆርም ወደ እሳቱ እቶን በመቅረብ እነዚህ
ብላቴኖችን “እናንተ የልዑል አምላክ ባሮች ሲድራቅና ሚሳቅ
አብደናጎም ኑ ውጡ ብሎ ተናገራቸው፡፡” እነርሱም ከእሳቱ
ወጡ ሹማምንቱና መኳንንቱ፣ አማካሪዎችና የአገር ገዢዎች
ሁሉ እሳቱ በእነዚህ ብላቴኖች ላይ አንዳች አቅም
እንዳልነበረው፣ ከጠጉራቸው ቅንጣት አንዱን እንኳ
እንዳላቃጠለው፣ ሰናፊናቸውም እንዳልተለወጠ፣ የእሳቱም ሽታ
እንዳልደረሰባቸው ተመለከቱ፡፡ ንጉሥ ናብከደነፆርም መልአኩን
ልኮ ያዳናቸውን የእነዚህን ቅዱሳንን አምላክ አመሰገነ፡፡
በእነርሱ አምላክ ላይም የስድብን ቃል የሚናገር ሰው
እንደሚገደልና ቤቱም የጉድፍ መጣያ እንዲሆን አዋጅ
አስነገረ፡፡ አዛርያ አናንያ ሚሳኤልም በንጉሡና በሹማምነቱ
ዘንድ ሞገስ አገኙ በክብርም ከፍ ከፍ አሉ፡፡(ዳን.3
ስለዚህም ቤተ ክርስቲያን መንጎቹዋ የእምነትን ፍሬ ከእነዚህ
ብላቴኖች ተምረው እግዚአብሔርን በማምለክ እንዲጸኑና
የመልአኩን የቅዱስ ገብርኤልን ተራዳኢነት እንዲረዱ
በታኅሣሥ 19 ቀን ይህን ዕለት ትዘክራለች፤ በታላቅ
ድምቀትም ታከብረዋለች፡፡ እንደ ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ
እምነት በድርጊት ሊታይ የሚገባው ክርስቲያናዊ ተግባር ነው፡፡
በክርስቶስ ኢየሱስ አምናለሁ የሚል ሁሉ ካመነበት ጊዜ አንስቶ
ክርስቶስን መስሎ ለመኖር ሊተጋና መስሎ ሊመላለስ
ይገባዋል፡፡ በሠልስቱ ደቂቅ የታየው እምነት በአንድ ጀምበር
የተገነባ እምነት ሳይሆን ከልጅነታቸው ጀምሮ በአንድ
እግዚአብሔር ታምነው በቅድስና ሕይወት በመመላለስ የመጣ
እምነት ነው፡፡ እነዚህ ብላቴኖች በእግዚአብሔር ዘንድ
የሚያገኙትን የድል አክሊል ተስፋ አድርገዋልና አርባ ዘጠኝ
ክንድ ያህል የነደደውን የእሳት እቶን አላስፈራቸውም፤
በእግዚአብሔር ላይ ያላቸው ጽኑ እምነት በእሳት ተቃጥለው
ለመሞት እንኳ አስጨከናቸው፡፡ እንዲህም ሆነው
በመገኘታቸው በእምነታቸው እግዚአብሔርን ደስ አሰኙት፤
ስለዚህም እግዚአብሔር ባለሟሉን ቅዱስ ገብርኤልን በመላክ
ከእሳቱ እቶን ታደጋቸው፡፡
የመልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ምልጃና ጸሎት ይጠብቀን
ወስብሐት ለእግዚአብሔር
ወለወላዲቱ ድንግል
ወለመስቀሉ ክቡር
ለዘለዓለሙ አሜን፡፡

Saturday, May 21, 2016

=>+*"+<+>#መልዐኩ_ቅዱስ_ሩፋኤል<+>+"*+

#መልዐኩ_ቅዱስ_ሩፋኤል
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን።
“እንግዶችን መቀበል አትርሱ፤ በዚህ አንዳንዶች ሳያውቁ
መላእክትን እንግድነት ተቀብለዋልና።” ዕብ.፲፫፡፩
ሩፋኤል ማለት ፈታሄ መሕፀን ማለት ነው። ሣልሳይ ሊቀ
መላእክት ነው። ለሄኖክ ወልደ ያሬድ 6 ዓመት በእግረ ገነት
ወድቆ ሳለ ህበዓቱን ክሡታቱን አሳይቶታል። መ/ሄኖክ 8፡5
ቅዱስ ሩፋኤል የጦቢትን ዓይን ያበራና ወለተ ራጉኤልን
ተቆራኝቷት ከነበረው ጋኔን ያላቀቃት መሆኑ በመጽሐፈ ጦቢት
በስፋት ተገልጿል፡፡ ቤቱንም በበረከት ሞልቶታል።
ጦቢት በፋርስ ንጉሥ በስልምናሶር ዘመን የተማረከ ከነገደ
ንፍታሌም የተወለደ ጽኑዕ እሥራኤላዊ ነው፡፡ እግዚአብሔር
በስልምናሶር ፊት የመወደድን ግርማና ባለሟልነትን ስለ
ሰጠው አለቃ አድርጎ ሾሞት ነበር፡፡ ለወገኖቹ ምጽዋት
በመስጠት ሕገ ርትዕን በመሥራት የተጋ ሰው ነበር፡፡ ሐና
የምትባል ሚስት አግብቶ አንድ ልጅ ወልዷል፡፡ ስልምናሶር
ሞቶ ሰናክሬም በነገሠ ጊዜ ከሹመቱ ስለሻረው ደግሞ ወደ
ምድያም መሔድ አልቻለም፡፡
ሣራ ወለተ ራጉኤል ከፍተኛ ችግር ደርሶባት ነበር፡፡ ችግሯም
ሕፃናት ወልጄ ቤት ንብረት ይዤ እኖራለሁ በማለት ባል
አገባች። ነገር ግን በዚች ሴት አስማንድዮስ የሚባል ጋኔን
አድሮ ያገባችውን ሰው ገደለባት ሌላም ባል ብታገባ ሞተባት
እንደዚህ እየሆነ በጠቅላላ ሰባት ድረስ ያሉትን ባሎችን
ገደለባት፡፡
የራጉኤል ልጅ ሣራ በዚህ ሁኔታ በኀዘን ተውጣ ስትኖር
በነበረበት ጊዜ ጦቢት ሸምግሎ ስለ ነበር ልጁ ጦብያን ጠርቶ
በዚህ ዓለም እስካለ ድረስ ሊሠራው የሚገባውን መንፈሳዊ
ሥራ እንዲሠራ በጥብቅ ከመከረው በኋላ በመጨረሻ ልጄ እኔ
ሳልሞት የኑሮ ጓደኛህን ፈልግ፣ ስትፈልግም ዕወቅበት፣ እኛ
የአብርሃም የይስሐቅና የያዕቆብ ዘሮች ነን ስለዚህ ከእነርሱ
ወገን የሆነችውን እንድታገባ ከዚህም ሌላ ከገባኤል ዘንድ
በአደራ ያስቀመጥኩት ገንዘብ አለና እኔ በሕይወት እያለሁ
ብታመጣው የተሻለ ነው አለው፡፡
ጦብያም ያባቱን ምክር ሁሉ በጽሞና ካዳመጠ በኋላ ‹አባባ
የነገርከኝን ነገር ሁሉ በተቻለኝ መጠን እፈጽማለሁ ግን
ከገባኤል ጋር ስላለው ገንዘብ እንዴት ለማምጣት እችላለሁ?
ሀገሩን አላውቀውም› አለው፡፡ በዚህ ጊዜ ነገሩ አሳሳቢ ሆኖ
ስላገኘው ጦቢት ልጁ ጦብያን ‹አብሮህ የሚሄድ ሰው እስቲ
ፈልግ ምናልባት አብሮ የሚሄድ ጓደኛ ታገኝ ይሆናል
ደመወዝም ሰጥተን ቢሆን ካንተ ጋር የሚሄድ አንድ ሰው ግድ
ያስፈልግሃልና ሂድ ሰው ፈልግ› አለው፡፡
አብሮት የሚሄደው ሰው ለመፈለግም ቢሄድ አንድ መልካም
ጐበዝ አገኘ ይኸውም መልአኩ ቅዱስ ሩፋኤል ነው፡፡ጦብያ ግን
መልአኩ ቅዱስ ሩፋኤል መሆኑን ፈጽሞ አላወቀም ነበር፡፡
ይሁን እንጂ ጦብያ መልአኩን ሰው መስሎ እንዳገኘው
‹የሜዶን ክፍል ወደ ምትሆነውና ራጌስ ወደ ምትባለው ሀገር
ከእኔ ጋር ለመሄድ ትችላለህን የድካምህን ዋጋ የጠየቅኸውን
ያህል እሰጥሃለሁ› ሲል ጠየቀው ቅዱስ ሩፋኤልም ‹እሺ ካንተ
ጋር ለመሄድ ፈቃኛ ነኝ መንገዱንም ሆነ ሀገሩን በሚገባ
አውቀዋለሁ ከገባኤል ቤት ብዙ ጊዜ ኑሬአለሁና› አለው፡፡
ከዚህ በኋላ ጦብያ በል ከአባቴ ጋር ላስተዋውቅህ ብሎ ወደ
አባቱ ወስዶ አስተዋወቀው ከእኔ ጋር የሚሄደው ሰው ይህ ነው
በማለት ካስተዋወቀው በኋላ ጦቢትም ከወዴት እንደ መጣ
ማን ተብሎ እንደሚጠራ ጠየቀው፡፡ መልአኩ ቅዱስ
ሩፋኤልም የታላቅ ወንድምህ ወገን ከመሆንም ሌላ ስሜም
አዛርያስ ይባላል አለው፡፡ ጦቢ. 5.12 ፡፡ ጦቢትም የወንድሙ
ዘመድ መሆኑን ከሰማ በኋላ ‹አንተስ ወንድሜ ነህ በል የልጄ
የጦብያን ነገር አደራ ከሀገር ወጥቶ አያውቅምና እንዳይደነግጥ
ደኅና አድርገህ እንድትይዝልኝ› ብሎ ስንቃቸውን አስይዞ
ሸኛቸው፡፡
አዛርያስ /ቅዱስ ሩፋኤል/ በመንገድ ይመራው ነበር፡፡ በዚህም
ቅዱስ ሩፋኤል ‹መራኄ ፍኖት› /መንገድ መሪ/ ይባላል፡፡
እነርሱ ሲሄዱ ውለው ማታ ጤግሮስ ከተባለው ታላቅ ወንዝ
ደረሱና ከዚያም ለማደር ወሰኑ፡፡ በዚህ ጊዜ ከድካሙ ጽናት
የተነሣ ጦብያ ሊታጠብ ወደ ወንዙ ወረደና ልብሱን አውልቆ
መታጠብ ሲጀምር አንድ ዓሣ ሊውጠው ከባሕር ወጣ፡፡
ወዲያውም መልአኩ ቅዱስ ሩፋኤል ጦብያን ያዘው ፤ ዓሣውን
እንዳትለቀው አለው ፤ ጦቢያም ከዓሳው ጋር ግብ ግብ ገጥሞ
እየጐተተ ወደ የብስ አወጣው ፡፡ከዚህ በኋላ ቅዱስ ሩፋኤል
ጦብያን እንዲህ ሲል አዘዘው፡፡ ዓሣውን እረደው ጉበቱንና
ሐሞቱን ተጠንቅቀህ ያዘው ሌላውን ግን ጠብሰን እንበላዋለን
አለው፡፡
ጦብያም መልአኩ እንዳዘዘው ዓሣውን አርዶ ሐሞቱንና ጉበቱን
ያዘ፣ ሌላውን ሥጋውን ግን ጠብሰው ራታቸው አደረጉት፡፡
ጦብያም ያንን የዓሣውን ጉበትና ሐሞት ለምን
እንደሚያገለግል ለመረዳት ‹ይህን ያዘው ያልከኝ ለምንድን
ነው?› ሲል ጠየቀው ቅዱስ ሩፋኤልም ጋኔን ያደረበት ሰው
ሲገኝ ይህንን ከዕጣን ጋር ቢያጤሱበት ጋኔኑ ይለቃል ሲል
መለሰለት፣፡
በዚህ ሁኔታ አንድ ባንድ ሲነጋገሩ ከቆዩ በኋላ መልአኩ ቅዱስ
ሩፋኤል ጦብያን ‹ዛሬ ከራጉኤል ቤት እናድራለን፡፡ እርሱ
ዘመድህ ነው፡፡ የእርሱም ልጅ ሣራ የምትባል ቆንጆ ልጅ
አለችው፡፡ እሷን ለሚስትነት ይሰጥህ ዘንድ ለራጉኤል
እነግርልሃለሁ› አለው፡፡
ጦብያም ‹ያች ልጅ ከዚህ በፊት ሰባት ሰዎች እንዳገቧትና
ሰባቱም ባገቧት ሌሊት ደርቀው /ሞተው/ እንደሚያድሩ
ሰምቻለሁ፡፡ ስለዚህ እኔ ላባቴና ለእናቴ አንድ ልጅ ነኝ እርስዋን
አግብቼ ከዚህ በፊት እንዳገቧት ሰዎች እኔም የሞትኩ እንደሆነ
አባቴንና እናቴን የሚረዳቸው የለም ቢሞቱም የሚቀብራቸው
አያገኙምና እፈራለሁ› አለው፡፡ መልአኩ ቅዱስ ሩፋኤል ግን
‹አባትህ ከዘመዶችህ ወገን ካልሆኑ በስተቀር ሌላ ሴት
እንዳታገባ ሲል የነገረህን ረሳኸውን? በል ሰባት ባሎቿ
ሙተውባታል ስለምትለው እኔ መድኃኒቱን አሳይሃለሁ ፤ አይዞህ
አትፍራ አትሞትም የዓሣውን ሐሞትና ጉበቱን ለምን መሰለህ
ያዘው ያልኩህ ? እንግዲህ ሐሞቱንና ጉበቱን ከዕጣን ጋር
ጨምረህ ስታጤስበት በሣራ አድሮ የነበረው አስማንድዮስ
የተባለው ጋኔን ወጥቶ ይሄዳል ፈጽሞም ወደ እርሷ በገባህም
ጊዜ ሁለታችሁ ይቅር ባይ ወደ ሆነው እግዚአብሔር ጸልዩ
እርሷም የተዘጋጀች ናት፡፡ ከእኛ ጋርም ወደ ሀገርህ ይዘናት
እንሄዳለን› አለው፡፡ ጦብያም ይህንን ቃል በሰማ ጊዜ ደስ
አለውና ከእርሷ በስተቀር ሌላ እንዳያገባ በሙሉ አሳቡ ወሰነ፡፡
ከዚህ በኋላ ወደ ራጉኤል ቤት እንደ ደረሱ ሣራ በደስታ
ተቀበለቻቸው የሣራ አባትም ጦብያን ገና እንዳለው ሚስቱ
አድናን ‹ይህ ልጅ የእኔ ዘመድ ጦቢትን ይመስላል› አላት
ከዚያም ጋር አያይዞ ‹ልጆች ከየት ሀገር መጣችሁ?› አላቸው፡፡
እነሱም ‹ከነነዌ ሀገር ነው የመጣን› አሉት፡፡ ‹ከዚያም ሀገር
ጦቢት የሚባል ወንድም ነበረኝ ታውቁት ይሆን?› ሲል
ጠየቃቸው፡፡ በዚህ ጊዜ ጦቢያ አባቱን ሲጠራለት
‹እናውቀዋለን፡፡ እኔም ራሴ የጦቢት ልጅ ነኝ› አለው፡፡ ከዚያ
በኋላ ራጉኤል ‹የወንድሜ ልጅ ነህን?› ብለ እቅፍ አድርጐ
ሳመው፡፡ አድናም ሳመችውና ሁሉም ተያይዘው የናፍቆት ልቅሶ
ተላቀሱ፡፡ ከወንድሙ እንደ መጡም ሲገነዘብ በግ አርዶ በጥሩ
ሁኔታ ጋበዛቸው፡፡
ትም ከበሉ በኋላ ጦብያ ቅዱስ ሩፋኤል በመንገድ የነገረውን
በልቡ ሲያወጣ ሲያወርድ ስለ ዋለ ቅዱስ ሩፋኤልን ያንን
በመንገድ የነገርከኝን አሁን ፈጽምልኝ ሲለው ሰምቶ ስለ ልጅቷ
መሆኑን ስለ ገባው ራጉኤል ጦብያን ‹ልጄ ይህች ልጅ ላንተ
የምትገባ ናት ሰጥቸሃለሁ አይዞህ አትጠራጠር አሁንም ብላ
ጠጣ ለዛሬም ደስ ይበልህ አለውና ሣራ ካለችበት የጫጉላ ቤት
አግብተው ዘጉት፡፡ ጦብያም ሣራን በይ እኅቴ ኑሮዋችን
እንዲቃናልንና ጋብቻችን እንዲባረክልን አስቀድመን ወደ
ፈጣሪያችን ጸሎት እናድርግ› አላትና አብረው ጸሎት ካደረጉ
በኋላ ያንን የያዘውንና የዓሣ ጉበትና ሐሞት ከዕጣን ጋር
ጨምሮ ቢያጤስበት በሣራ አድሮ ባሎችዋን ይገድልባት
የነበረው አስማንድዮስ የተባለው ጋኔን ከሣራ ለቆ ወጥቶ ሄደ
ሁለተኛም ሊመለስ አልቻለም፡፡ እነርሱም በሰላምና በጤና
አደሩ፡፡ የጦብያንና የሣራን ጋብቻ የባረከ ቅዱስ ሩፋኤል ስለሆነ
‹መልአከ ከብካብ› ይባላል፡፡
ከዚያ በኋላ የጤንነታቸውን ነገር ሲረዱ የሰርጉ ቀን የሚሆን
የ14 ቀን በዓል እስኪፈጸም ድረስ ጦብያ ወደ ሀገሬ እሄዳለሁ
ብሎ እንዳያውከው በማለት አማለው፡፡
የ14 ቀን በዓለ መርዓ ከተፈጸመ በኋላ ግን ጥሬ ገንዘብና
የከብት ስጦታ አድርጐ መርቆ ወደ ሀገሩ ሰደደው፡፡ ወላጆቹ
ጦቢትና አድና ግን በመዘግየቱ ልጃችን ምን አግኝቶት ይሆን?
እያሉ ለጊዜው ሳያዝኑ አልቀሩም፡፡ ከጥቂት ቀናት በኋላ
ሚስቱንና ግመሎቹን ይዞ ሲመጣ በክብርና በደስታ ተቀበሉት፡፡
የጦብያ አባት ጦቢትም ልጅህ መጣ ሲሉት ዓይነ ሥውር ስለ
ነበር እርሱን እቀበላለሁ ሲል ስለ ወደቀ ወዲያው ጦብያ
የዓሣውን ሐሞትና ጉበቱን ይዞ ስለ ነበር የአባቱን ዓይን ቀባው
ወዲያውም ዓይኖቹ ተከፈቱ፡፡
በመጨረሻም ከጦብያ ጋር ሄዶ የነበረው መልአኩ ቅዱስ
ሩፋኤልን የድካሙን ዋጋ ገንዘብ ለመስጠት ጠሩት እርሱ ግን
ጦቢትንና ጦብያን ‹ፈጣሪያችሁን አመስግኑ እናንተ እስከ ዛሬ
ድረስ ከየት እንደመጣሁ ማን እንደ ሆንኩ አላወቃችሁኝም፡፡
የእግዚአብሔር ምሥጢር ግን በክብር ሊገለጥ ይገባል እንጂ
ሊሰውሩት ስለማይገባ የእኔን ተፈጥሮና ስም ልነግራችሁ
እፈልጋለሁ ተፈጥሮዬ መልአክ ነኝ፣ ሥራዬም የቅዱሳንን ጸሎት
ከሚያሳርጉ ከሰባቱ ሊቃነ መላእክት አንዱ እኔ ሩፋኤል ነኝ›
ሲል ገለጠላቸው፡፡ እነርሱም ወድቀው የአክብሮት ስግደት
ሰገዱለት፡፡ የአባቶቻቸውን አምላክ እግዚአብሔርንም
አመሰገኑት፡፡ /መጽ. ጦቢት/፡፡
ስለዚህ እንግዶችን መቀበል አንርሳ፡፡ በዚህም ምክንያት
አንዳንዶች ሳያውቁ የመላእክትን እንግድነት ተቀብለዋልና፡፡
ዕብ. 13.1-2 ፡፡
ጦቢት ከእህሉ ከፍሎ ለተራበ የሚያበላ ከልብሱ ለተራቆተ ሰው
የሚያለብስ እግዚአብሔርን ዘወትር የሚያመሰግን ለወገኖቹ
የሚራራ አሥራት በኩራት የሚያወጣ ሰው ነበር፡፡ በመሆኑም
በሥራው ሁሉ እንዲረዳው በችግሩ ጊዜ እንዲያጸናው ቅዱስ
ሩፋኤል ተልኮለታል፡፡ እኛም በሕይወታችን የጐደለብንን ነገር
እንዲሞላልን ጐዳናችንን እንዲያስተካክልልን ከክፉ ጋኔን
እንዲጠብቀን አምላክ ቅዱስ ሩፋኤል ተለመነን ቅዱስ
ሩፋኤልንም አማልደን ማለትን ገንዘብ እናድርግ፡፡
ጳጉሜ የዘመን መሸጋገሪያ እንደ ሆነች ዕለተ ምጽአትም ወደ
እግዚአብሔር መንግሥት የምንሸጋገርባት ስለሆነች ከወዲሁ
የቅዱስ ሩፋኤልን የመታሰቢያ በዓሉን ስናከብር በአማላጅነቱ
ከቅዱሳን ኅብረት እንዲደምረን በንስሐ ታጥበን ደጅ ልንጠና
ይገባል፡፡
የሊቀ መልአኩ የቅዱስ ሩፋኤል ምልጃው፣ ጥበቃውና
ቃልኪዳኑ ይደረግልን በረከቱ ይደርብን፡፡ አሜን፡፡
ልመናው ከእኛ ከሀገራችንም ከኢትዮጵያ ጋር ለዘላለሙ ጸንቶ
ይኑር።
“ስብሐት ለእግዚአብሔር ለዘአብጽሐና እስከ ዛቲ ሰዓት”
ወስብሔት ለእግዚአብሔር ወለ ወላዲቱ ድንግል ወለ መስቀሉ
ክቡር አሜን ይቆየን።

=>+*"+<+>ቅዱስ ሩፋኤል<+>+"*+

#ቅዱስ_ሩፋኤል
#ከከበሩት_ከ_ሰባቱ_ሊቃነ _መላእክት_አንዱ
#እኔ_ሩፋኤል_ነኝ ::
ጦቢት 12 : 13
እንግዲህ ከባህሪው ቅድስና ፍጥረቱን በጸጋ ቅድስና መርጦ
የሚለይ እግዚአብሔር አክብሮ እንዲህ ያለ ሰማያዊ ፀጋ
ከሰጣቸው ቅዱሳን መላእክት መካከል በስልጣኑ ሊቀመናብርት
(የመናብርት አለቃ) የሆነ በሹመት ፈታሔ ማኅጸን (ማሕጸን
የሚፈታ) ከሳቴ እውራን (የእውራንን ዓይን የሚያበራ) ሰዳዴ
አጋንንት (አጋንንትን የሚያባርር) ፈዋሴ ዱያን (ድውያንን
የሚፈውስ)፣ አቃቤ ኆኅት (የምህረትን ደጁ የሚጠብቅ) ተብሎ
የተገለጠ ከሊቃነ መላእክቱ ቅዱስ ሚካኤልና ቅዱስ ገብርኤል
ተከትሎ የሚነሳ መልአክ ራሱን እንዲህ በማለት ገለጠ «
የቅዱሳንን ጸሎት ከሚያሳርጉ ወደ ከበረ ወደ ገነነ ወደ
እግዚአብሔር ጌትነት ከሚያገቡ ከከበሩ ከሰባቱ አለቆች አንዱ
አለቃ እኔ ሩፋኤል ነኝ» (ጦቢ.12÷15)
ይህ የከበረ ታላቅ መልአክ ሰሙ የእብራይስጥ ሁለት ቃላት
ጥምረት ውጤት ነው፡፡ ሩፋ ማለት ጤና፣ ፈውስ፣ መድኃኒት
ማለት ሲሆን ኤል ሚለው በሌሎቹም መላእክት ስም ላይ
የሚቀጠል ስመ አምላክ ነው ይህም « መልአኬን በፊትህ
እሰዳለሁ….. ስሜ በእርሱ ስለሆነ .
አታስመርሩት» (ዘጸ.23÷20-22) እዳለው ነው፡፡
ታዲያ ሩፋኤል የሚለው በጥምረት ከአምላክ ለሰዎች የተሰጠ
ፈውስ የሚለውን ይተካል «በሰው ቁስል የተሾመ ከከበሩ
ከመላእክት አንዱ ሩፋኤል ነው፡» (ሄኖ.6÷3)
ይህ መልአክ እንደሌሎቹ ሊቃነ መላእክት ሁሉ የሰው ልጆችን
ይጠብቃቸዋል(ዳን.4÷13 ዘጸ. 23÷20 መዝ.
90÷11-13 )
ያማልዳል፣ ከፈጣሪ ያስታርቃቸዋል፡፡(ዘካ.1 ÷12)
በፈሪሀ እግዚአቤሔር እና በአክብሮተ መላእክት ያሉትን
ድናቸዋል (ዘፍ.49÷15 መዝ.3÷37)
« እግዚአብሔር ሃይሉን የሚገልጥበትን ቅጣቱን ሊያሳይ ቢወድ
አስቀድሞ መርጦ በወደዳቸው ለይቅርታ የተዘጋጁ የይቅርታ
መላእክትን ያመጣል» (ሮሜ.9÷22)
ቅዱስ ሩፋኤል ሊቀመናብርትን ድንቅ ገቢር ተአምራቱን ያዩ
ምዕመናን
……የወላድ ማኅፀን እንዲፈታ
ስለተሸመ ከጌታ
አዋላጅ ብትኖር ባትኖርም
ሐኪም ሩፋኤል አይታጣም
በምጥ ጊዜ ሲጨነቁ የባላገር ሴቶች ሁሉ
የመልአኩን መልክ አንግተው ማርያም ማርያም ይላሉ
ማየጸሎቱን ጠጥተው ቶሎ ፈጥነው ይወልዳሉ ……
እያሉ ደጅ ጠንተው ይማጸኑታል፡፡
ዜና ግብሩን ሊቁ ዮሐንስ አፈወርቅ ከተናገረለት በመነሳት
በቅዱሳን ላይ ድንቅ የሆነ እግዚአብሔር በመልአኩ አድሮ
ያደረጋቸውን ተግባራት አበው የበረከት ምንጭ በሆነ ድርሳኑ
ላይ አኑረው የበረከቱ ተካፋይ እንድንሆን ሰጥተውናል፡፡ በጉልህ
ሠፍረው ከምናገኛቸው ብዙ ድንቅ ሥራዎች መሀል ጥቂቶቹን
እነሆ
~~~> በሥነ-ስዕሉ የተማጸኑ፣ በምልጃው ታምነው የጸኑ
ቴዎዶስዮስንና ዲዮናስዮስን በገሃድ ተገልጾ ለንግስናና ለጵጵስና
ክብር አብቅቷቸዋል፡፡
~~~> የንጉስ ቴዎዶስዮስ ልጅም ጻድቁ አኖሬዋስም
በፈጣሪው ህግ እየተመራ የሊቀ መናብርቱን መታሰቢያ ቤተ
መቅደስ አሳንጾ ሲያስመርቅ ለበለጠ ክብር ልቡን አነቃቅቶ
ለታናሽ ወንድሙ ለአርቃዴዋስ የነጋሢነት ስልጣኑን ትቶ መንኖ
በስውርና በጽሙና እዲኖር ረድቶታል፡፡
~~~> በሊቀጳጳሳት ቴዎፍሎስ ዘመን አባቶች ለሊቀመናብርቱ
ክብር በአሣ አንበሪ ጀርባ ላይ ያሳነጹትን መታሰቢያ ቤተ
መቅደስ በወደቡ አጠገብ በእስክንድሪያ ሳለች ጠላት ዲያቢሎስ
አነዋውጾ ለምስጋና የታደሙትን ምዕመናን ሊያጠፉ አሣ
አንበሪውን ቢያውከው ወደ ሊቀመናብርቱ ተማጽነው እርዳን
ቢሉ ፈጥኖ ደርሶ በበትረ መስቀሉ (ዘንጉ) ገሥጾ ከጥፋት
ታድጓቸዋል፡፡
በቅዱስ መጽሐፍም እንደተገለጠው
~~~> ሣራ ወለተ ራጉኤልን አስማንድዮስ ከተባለው የጭን
ጋንኤን ሲታደጋት የጦቢያን አባት የጦቢትን ዓይን አበራለት
(መጽሐፍ ጦቢት)
ከዚህም አልፎ የይስሐቅን እናት ሣራን፣ የሶምሶንን እናት
(እንትኩይን) ምክነታቸውን የቆረጠ ወልዶ ለመሳም ያበቃቸው
ይኸው ፈታሔማኅጸን የልዑል እግዚአብሔር መልአክተኛ ቅዱስ
ሩፋኤል ነው፡፡ከመልአኩ ከቅዱስ ሩፋኤል ረድኤት ያሳድርብን
አሜን !!!

=>+*"+<+>◆ ቅዱስ ሩፋኤል + አቡነ ዘርዓ ብሩክ ◆<+>+"*+

◆ ቅዱስ ሩፋኤል + አቡነ ዘርዓ ብሩክ ◆
ፈታሄ ማህጸን ቅዱስ ሩፋኤል
ለዘጠና ዘጠኙ ነገደ መላእክት ሰባት አለቆች አሏቸዉ፡፡እነዚህ
የተመረጡ ሊቃነ መላእክት ለተልእኮ ፤ለምስጋና ፤ለማማለድ
በቧለማልነት ዘወትር በእግዚአብሔር ፊት የሚቆሙ
ናቸዉ፡፡‹‹‹ርኢኩ ሰብዐተ መላእክትተ እለ ይቀዉሙ ቅድመ
እግዚአብሐየር ሰባት ሊቃነ መላኢክት በእግዚአብሐየር ፊት
ቆመሁ አየሁ ››››እንዲል ራእ 8፡2፡፡ከእነዚህ ሊቃነ መላኢክት
አንዱ ቅዱስ ሩፋኤል ሲሆን በማእረግ ሦስተኛ ነዉ፡፡በሰዉ
ቁስል የተሸመ ፤በፈዉስ ላይ የተሸመ፤ ከከበሩ መላእክት አንዱ
ቅዱስ ሩፋኤል ነዉ፡፡ሄኖክ 6፡3 ፡፡ቅዱስ ሩፋኤል ራሱም
‹‹‹የቅዱሳንን ጸሎት ከሚያሳርጉ ወደ ከበረ ወደ ገነት ወደ
እግዚአብሐሔር ጌትነት ከሚያ...ስገቡ ሰባት አለቆች አንዱ
ቅዱስ ሩፋኤል ነኝ ብሎል፡፡ጦቢት 12፡15 እግዚአብሔርም
በሃያ ሦስቱ ነገደ መላእክትም ላይ ሾሞታል፡፡
ቅዱስ ሩፋኤል ሰማያዉያን መዛግብት በእጁ የሚጠበቁ
በመሆናቸዉ‹‹ዐቃቤ ኖኀቱ ለአምላክ ›››ይባላል፡፡እግዚአብሔ
ር እንዳዘዘዉ የሚከፍታቸዉ የሚዘጋጋቸዉ እርሱ ቅዱስ
ሩፋኤል ነዉ፡፡በዚያች በድህነትና በደስታ ቀን ለሕዝበ ክርስቲያን
ከዕፀ ህይወት ይሰጣቸዉ ዘንድ እግዚአብሔር ያዘዘዉ ቅዱስ
ሩፋኤልን ነዉ፡፡ይህ የከበረ መላእክት ‹‹‹ፈታሄ ማህጸን››››
ይባላል፡፡እናቶች ሲወልዱ ምጥ እንዳይበዛባቸዉ የሚራዳ
መልአክ ነዉ፡፡በመሆኑም አያሌ ክርስቲያኖች ማርገዛቸዉን
ካወቁ ጀምሮ ድርሳኑን በማንበብ መልኩን በመድገም ጠበሉን
በመጠጣት ሰዉነታቸዉን በመቀባት ይለምኑታል፡፡እንደ
እምነታቸዉ ጽናት ይደረገላቸዋል፡፡
◆◆◆+++ አቡነ ዘርዓ ብሩክ +++
የጻድቁ አባታችን የዘርዓ ብሩክ አባት እና እናት የተባረኩ
ከቅዱሳን ወገን የሚሆኑ ነበሩ የአባታቸው ስምም ቅዱስ ደመ
ክርስቶስ ሲባል እናታቸው ደግሞ ቅድስት ማርያም ሞገሳ
ትባላለች ጻድቁ አባታችን ገና በናታቸው ማህጸን እያሉ ነበር
ብዙ ተአምራት የሚያደርጉት እግዚአብሄር መርጡአቸዋልና
በሁአላም ከክርስቶስ ልደት በሁአላ በስምንተኛው መቶ ክ/
ዘመን መጨረሻ ላይ በነሃሴ 27 ጻድቁ አባታችን ተወለዱ
በ40ኛ ቀናቸውም ተጠምቀው በካህናት አፍ "ጸጋ ክርስቶስ"
ተባሉ ከዛም ቤተሰቦቻቸው በጥሩ እድገት አሳደጉአቸው 7
አመትም በሞላቸው ግዜ በልጅነቴ የዚን አለም ክፋቱን
እንዳላይ ብለው ቢጸልዩ አይናቸው ታውሩአል:ቤተሰቦቻቸውም
የዚን አለም ትምህርት ሊያስተምሩአቸው አስተማሪ ጋር
ቢወስዱአቸው ታመው ተመልሰዋል:የእግዚአብሄር ፈቃድ
አይደለምና ነገር ግን የሚያስፈልጋቸውን እውቀት ፈጣሪ
አምላክ ራሱ ገልጾላቸዋል:: ክህነትን እስከ ጵጵስና እራሱ
መድሃኒአለም ክርስቶስ ሰቶአቸዋል:12 አመትም በሞላቸው
ግዜ አይናቸው በርቶላቸው ታላላቅ ተጋድሎን ማድረግ ጀመሩ :
የሃጥያት ማሰርያን ያስሩና ይፈቱ ዘንድ ጵጵስናን በሾማቸው ግዜ
እግዚአብሄር ያወጣላቸው ሁለተኛ ስም "ዘርዓ ብሩክ" ይባል
ነበር 3ኛውም ስማቸው ደግሞ "ጸጋ እየሱስ"ይባላል:: ጻድቁ
አባታችን በዚ አለም በህይወተ ስጋ ሳሉ አቡቀለምሲስ
እንደሚባል እንደ ዮሃንስ ወልደነጎድጉአድ እግዚአብሄር እሱ
ወዳ...ለበት ወደ ሰማይ አውጥቶ በገነት መካከል ያኖራቸው
ነበር:: እግዚአብሄር አምላክ ለወዳጁ ለብጹዕ አባታችን ዘርዓ
ብሩክ በጎ ነገር እንዳደረገለትና ያለ ድምጽ የሰማይ ደጆችን
አልፎ የእሳት ባህርን ተሻግሮ ፈራሽ በስባሽ ሲሆን እንደ ህያዋን
መላእክት በፍጥነት ከጽንፍ እስከ ጽንፍ ከአድማስ እስከ አድማስ
ይደርስ ዘንድ 12 ክንፍን ሰጣቸው:መላእክትም ለሌሎች
ቅዱሳን ያልተሰጠ ይህንን ስልጣን አይተው ለምድራዊ ሰው ይህ
ነገር እንዴት ይቻላል እያሉ አደነቁ: ከዛም በሁአላ ጻድቁ
አባታችን ከፈጣሪ ዘንድ የመላእክትን አስኬማ,የሾህ አክሊል
አምሳያ የሆነውን መንፈሳዊ ቆብን,ሰማያዊ ቅናትን እና የደረት
ልብስን(ስጋ ማርያም) ተቀብሎ በጾም እና በጸሎት በልመና
እና በስግደት እግዚአብሄርን ሲያገለግል ኖረ ከዛም በላይ
ወንጌልን እጅግ ብዙ በማስተማር ደከመ ከኢትዮጵያም አልፎ
ግብጽ ድረስ ገባ የእስክንድርያውን ሊቀ ፓፓስ አባ ዮሃነስን
አገኘውና እርስ በርስ ሰላምታን ተለዋውጠው እጅ ተነሳሱ
ከዛም ተመልሶ ወደ ሃገሩ መጣ ከዛም ኢትዮጵያ ውስጥ
እየተመላለሰ ወንጌልን አስተማረ እጅግ ስጋን በሚያስጨንቅ
ትጋትም የኢትዮጵያን ህዝብ ማርልኝ እያለ እያለቀሰ ይጸልይ
ነበር: አንድ ቀን አባታችን በንጉስ ጭፍሮች ተይዘው ሲሄዱ
ዳዊታቸውን ለግዮን ወንዝ አደራ ሰተዋት ከ5 አመት በሁአላ
ሲመለሱ ግዮን ሆይ ዳዊቴን ግሺ መልሺሊን ቢሉአት አንድም
የውሃ ጠብታ ሳይኖርባት ዳዊታቸውን ብትመልስላቸው ለደቀ
መዝሙራቸው ዘሩፋኤል አሳዩትና ግዮንንም "ግሽ አባይ"
ብለውታል እስካሁንም በዚሁ ስም የሚጠራው ከዚ በመነሳት
ነው:: ከዚህም ሌላ ጻድቁ አባታችን በዚሁ ወንዝ አካባቢ ለ 30
አመት ሲጸልዩ ፈጣሪ አምላክ ጸሎታቸውን ሰምቶ እጅግ ልዩ
የሆነ ቃል ኪዳን ሰቶአቸዋል:በስተመጨረሻም የሚያርፉበት
እለት በደረሰ ሰአት መልአከ ሞት መቶ እስኪደነግጥ እና ወደ
ሁአላው እስኪያፈገፍግ ድረስ ነው ነው እግዚአብሄር ጸጋውንና
ክብሩን ያበዛላቸው: በስተመጨረሻም ጥር በገባ በ13 ቀን
በ482 አመታቸው ስጋቸው ከነፍሳቸው ተለይታ ገነትን
ወርሰዋል::ምንጭ ገድለ አቡነ ዘርዓ ብሩክ የጻድቁ አባታችን
ገድለ ዜና እንኩአን በዚች በምታህል ጽሁፍ አይደለም
የገድላቸውም መጽሃፍም አልበቃውም እንደው እግዚአብሄር
አምላክ ከበረከታቸው እንዲያሳትፈን አስቤ ይችን ጥቂት
የገድላቸውን ዜና ከገድላቸው መጽሃፍ ላይ
አስቀመጥኩ:ለእግዚአብሄር ምስጋና ይሁን እኛንም በኚህ
ጻድቅ ጸሎት ይማረን በረከታቸውንም ያድለን አሜን
የቅዱስ ሩፋኤል ልመናዉ በረከቱ ይደርብን ፡፡አሜን ፡

Thursday, May 19, 2016

=>+*"+<+>ግንቦት 12<+>+"*+

አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
አሜን
ግንቦት 12-ዓሥር ታላላቅ ቅዱሳን በዓመታዊ በዓላቸው
ታስበው ይውላሉ፡፡
+ሐዲስ ሐዋርያ ብርሃን ዘኢትዮጵያ አቡነ ተክለ ሃይማኖት
ፍልሠተ ዐፅማቸው ነው፡፡
+ከ57 ዓመት በኋላ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ተገልጠውላቸው
‹‹...ጌታችን የነገረኝ ጊዜ ደርሷልና ሥጋዬን ከዚህ አፍልሰህ
አውጣ›› ብለው ስለ ፍልሠተ ዐፅማቸው የነገሯቸው አቡነ
ሕዝቅያስ ዕረፍታቸው ነው፡፡
+የዓለም ሁሉ መምህር የሆነ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ዕረፍቱ
ነው፡፡
+በኢየሩሳሌም አገር በጎልጎታ ላይ ከፀሐይ በልጦ በሚበራ
ብርሃን የከበረ ቅዱስ መስቀል መገለጥ ሆነ፡፡
+እናታችን ቅድስት ክርስቶስ ሠምራ እልፍ ነፍሳትን ከሲኦል
ያወጣችበት ዕለት ነው፡፡
+ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል ነቢዩ ዳንኤልን የረዳበት
ዕለት ነው፡፡ ዳንኤል በጉድጓድ ተጥሎ ሳለ መልአኩ ነቢዩ
ዕንባቆምን ነጥቆ ወስዶ ዳንኤል ካለበት አድርሶት
እንዲመግበው አደረገው፡፡
+ሃይማኖቱ የቀና የኢትዮጵያው ንጉሥ የበእደ ማርያም ልጅ
ጻድቁ ንጉሥ እስክንድር ዕረፍቱ መሆኑን ስንክሳሩ በስም
ይጠቅሰዋል፡፡
+ሰማዕታት የሆኑ ዲያቆን ሚናስና እስጢፋኖስ መታሰቢያ
በዓላቸው መሆኑን ስንክሳሩ በስም ይጠቅሳቸዋል፡፡
+በአባታችን በተክለ ሃይማኖት መንበር ከተሾሙት የከበሩ
መምህራን 17ኛ የሆነ የደብረ ሊባኖስ መምህር የከበረ አባ
አብርሃም ዕረፍቱ መሆኑን ስንክሳሩ በስም ይጠቅሰዋል፡፡
+የመላልኤል ልጅ የያሬድ የዕረፍቱ መታሰቢያ ነው፡፡ ያሬደም
162 ዓመት ኖሮ ኄኖክን ወለደው፡፡ ኄኖክንም ከወለደው በኋላ
800 ዓመት ኖሮ ወንዲችንና ሴቶች ልጆችን ወለደ፡፡ መላ
ዘመኑም 962 ዓመት በሆነው ጊዜ በዕለተ ዐርብ በሦስት ሰዓት
ዐረፈ፡፡
የዓለም ሁሉ መምህር የሆነ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ፡-
የዓለም ሁሉ መምህር የሆነ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ሀገሩ
ግሪክ ሲሆን አባቱ አስፋኒዶስ ወታደር ነበር፡፡ እናቱ አትናስያም
እንዲማርላት አቴና አስገባችው፡፡ እርሱም በሚገባ ተምሮ
አድጎ እነ ቅዱስ ባስልዮስ ካሉበት ገዳም ገባ፡፡ በዚያም ሳለ
አባትህ ሞተ ብለው ቢነግሩት ሄዶ የአባቱን ንብረት በሙሉ ሸጦ
ለድኆች ሰጥቶ ወደ ገዳሙ ተመልሶ በታላቅ ተጋድሎ መኖር
ጀመረ፡፡ መልአኩም ተገልጦለት ታየውና ‹‹አይዞህ አትፍራ
በርታ አሁን የአንጾኪያው ሊቀ ጳጳስ አቡነ ፊላታዎስ ወደ አንተ
ይመጣል›› ብሎት ተሰወረ፡፡ መልአኩ ለሊቀ ጳጳሱም ተገልጦ
‹‹ዮሐንስን ዳንኤል ሐዲስ›› ብለህ ስም አውጣለት ብሎታል፡፡
እርሱም አመንኩሶት ስሙን አውጥቶለታል፡፡
ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ምግብ ሲመገብ ገብሱን ከነአሰሩ
ይገብ ነበር እንጂ የላመ የጣፈጠ ቀምሶ አያውቅም፡፡
የቍስጥንጥንያው ሊቀ ጳጳስ ሲያርፍ በምትኩ ቅዱስ ዮሐንስ
አፈወርቅ በ397 ዓ.ም ተሾመ፡፡ በዚህ ጊዜ የነበረው ንጉሥ
አርቃድዮስ ከዮሐንስ አንደበት የሃይማኖትን ነገር ይማር ነበርና
አንድ ቀን ንጉሡ በወንጌል ላይ ስለ እመቤታችን የተጻፈውን
‹‹ጌታችንን እስክትወልድ ድረስ አላወቃትም›› የሚለውን ንባብ
ትርጉሙን አስፍቶና አብራርቶ ሲያስተምረው ንጉሡም አምኖ
ተደሰተ፡፡ በዚህም ጊዜ የእመቤታችን ሥዕል በሰው አንደበት
ሦስት ጊዜ ዮሐንስ አፈወርቅ፣ ዮሐንስ አፈወርቅ፣ ዮሐንስ
አፈወርቅ ብላ ስትጠራው እርሱም ሲመልስላት በተራው ሦስት
ጊዜ እሰግድ ለኪ እሰግድ ለኪ እሰግድ ለኪ በማለት አመስግኖ
ሰግዶላታል፡፡ ይህም በተአምረ ማርያም መግቢያ ላይ
ተመዝግቦ ተአምሯ ሲነበብ ምእመናን እንደ ዮሐንስ አፈወርቅ
እሰግድ ለኪ ይሏታል፡፡
አንድ ቀን ዮሐንስ አፈወርቅ አንዲት ሕፃን ልጅን ክርስትና
ሊያነሳ ሲሄድ መልአከ ሞት ደግሞ ሕፃኗን ሊቀስፍ ሲሄድ
በመንገድ ላይ ተገናኙና ዮሐንስ ‹‹ወዴት ትሄዳለህ?›› አለው፡፡
መልአከ ሞቱም ‹‹ሕፃኗን በሞት ቅሰፍ ተብዬ ተልኬ ልቀስፍ
እየሄድኩ ነው›› አለው፡፡ ዮሐንስም ‹‹ሳትጠመቅና ልጅነትን
ሳታገኝ እንዳትቀስፋት እስካጠምቃትም ድረስ
እንዳትንቀሳቀስ›› ብሎ በሥልጣነ ክህነቱ አስሮት ሄደና ሕፃኗን
ካጠመቃት በኋላ እረስቶት በሌላ መንገድ ተመለሰ፡፡ መልአከ
ሞቱም በዮሐንስ ሥልጣነ ክህነት ታስሮ 10 ዓመት እንደቆመ
ቆይቷል፡፡ ከ10 ዓመት በኋላ ዮሐንስ በዚያ መንገድ ሲያልፍ
መልአከ ሞትን ቆሞ ሲያየው ‹‹ለምን ጉዳይ ቆመሃል?››
አለው፡፡ መልአከ ሞትም ‹‹የዛሬ 10 ዓመት አንተ ስትሄድ
እንዳትንቀሳቀስ ስላልከኝ ሥልጣንህ እንደሰንሰለት አስሮ
ይዞኛል›› ቢለው ዮሐንስም ይህን ያህል ጊዜ በመርሳቱ ተጸጽቶ
‹‹ተሳስቻለሁ በል ሂድ ግብርህን ፈጽም›› ብሎት መልአከ
ሞትም ሄደና ልጅቱን ቀስፎ ዐርጓል፡፡ ዮሐንስም እቦታው
ሲደርስ ቤተሰቦቿ ሲያለቅሱ ቢያገኛቸው አስጽናቷቸው
ተመልሷል፡፡
ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ነገረ ሃይማኖትን እጅግ አስፍቶና
አምልቶ ያስተማረ እጅግ ሊቅ የሆነ የቤተ ክርስቲያናችን
መመኪያ ነው፡፡ በስሙ የተጠራውን ቅዳሴ ጨምሮ በጣም
በርካታ ድርሰቶችን ደርሷል፡፡ በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ዘመን
የነበረችው ጨካኟና አረመኔዋ ንግሥት አውዶክሲያ የድሃ
ንብረት እየቀማች ተወስድ ስለነበር ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅም
ዘወትር ይመክራትና ይገሥጻት ነበር፡፡ አንድ ቀን አንዱ ድሃ ሄዶ
ለዮሐንስ አፈወርቅ ነግሮት ሄዶ ‹‹የድሃውን ንብረት
መልሺለት›› ቢላት እምቢ ስትለው ከቤተ ክርስቲያን
እንዳትገባና ከክርስቲያኖችም ህብረት እንዳትቀላቀል
አወገዛት፡፡ ‹‹ከግዝትህ ፍታኝ›› ብትለውም ‹‹የድሃውን ገንዘብ
ካልመለሽ አልፈታሽም›› ስላላት ‹‹በከንቱ አወገዘኝ አባት
ያስተምራል እንጂ እንዲህ አያደርግም›› እያለች ታስወራበት
ጀመር፡፡ ለቅዱስ ኤጲፋንዮስም ‹‹ዮሐንስ ያለ አግባብ
አውግዞኛልና መጥተህ አስፈታኝ አለዚያ ሃይማኖቴን
እቀይራለሁ፣ ቤተ ክርስቲያንንም አቃጥላለሁ›› ብላ ላከችት፡፡
ቅዱስ ኤጲፋንዮስም ሄዶ ‹‹ሰይጣን በልቧ አድሮባታል
ያሰበችውንም ያስፈጽማታልና ለአገልግሎታችንም እንቅፋት
እንዳትሆን ፍታት›› ቢለው ቅዱስ ዮሐንስም እምቢ አለው፡፡
እርሷም በየከተማው እየዞረች ‹‹ተመልከቱ ዮሐንስ
ኤጲፋንዮስንም አወገዘው›› እያለች በውሸት ታስወራ ጀመር፡፡
ኤጲፋንዮስም እንዲህ ማለቷን አልሰማም ነበርና ከዮሐንስ ጋር
በኋላ ተሰነባብተው ሊለያዩ ሲሉ ዮሐንስ ‹‹ለምን በነገሬ
ገባህብኝ›› አለው፡፡ ኤጲፋንዮስም ‹‹አልገባሁም›› ቢለው
በንግግር ሳይግባቡ ቀርተው ተጣሉ፡፡ በዚህም ጊዜ ሁለቱም
የሚሞቱበት ጊዜና የሚሞቱበት በምን ዓይነት ሁኔታ እንደሆነ
ተገልጦላቸው አንዳቸው ለአንዳቸው ትንቢት ተነጋግረዋል፡፡
ዮሐንስ ኤጲፋንዮስን ‹‹ሄደህ ከቤትህ አትገባም ከመንገድ ላይ
አንበሳ ሰብሮ ይገድልሃል›› አለው፡፡ ኤጲፋንዮስም ለዮሐንስ
‹‹የእኔን ትላለህ አንተም እንጂ ደግሞ ተግዘህ በከሃዲዮች
ተወግዘህ በአንጾኪያ ደሴት ታስረህ ተሠቃይተህ ትሞታለህ››
አለው፡፡
በተነጋገሩትም ትንቢት መሠረት ኤጲፋንዮስ ወደ በዓቱ ሲሄድ
አንበሳ ገደለውና የአንበሳ ሆድ መቃብሩ ሆነለት፡፡ ዮሐንስም
በግዞት ታስሮ ብዙ ከተሠቃየ በኋላ ግንቦት 12 ቀን ዐረፈ፡፡
ጨካኟና አረመኔዋ ንግሥት አውዶክሲያም ‹‹ዮሐንስ
ኤጲፋንዮስን አውግዞት ወደ ሀገሩ አባሮት በመንገድ ላይ
እንዲሞት አደረገው›› እያለች በሀሰት አስወርታ የቤተ
ክርስቲያን ጠላቶች የሆኑትን ሰዎች ሰብስባ ዮሐንስን
እንዲያወግዙት ካደረገች በኋላ በግዞት ታስሮ እንዲኖርና
ተሠቃይቶ እንዲሞት አድርጋዋለች፡፡ ረድኤት በረከቱ ይደርብን፣
በጸሎቱ ይማረን፡፡
+ + + + + + + + + + + + + + +
ዳግመኛም በዚህች ዕለት እናታችን ቅድስት ክርስቶስ ሠምራ
እልፍ ነፍሳትን ከሲኦል አውጥታለች፡፡ ሊቀ መላእክት ቅዱስ
ሚካኤል በስሙ የተቀረጸ ጽላት አምጥቶ ለቅድስት ክርስቶስ
ሠምራ ሰጣትና በጓንጉት ደሴት ውስጥ በእርሱ ስም ቤተ
ክርስቲያን እንድታሠራ ነገራት፡፡ ‹‹እንዴት ይሆንልኛል?››
ባለችውም ጊዜ ‹‹እኒያ ያጠመቁሽ ቅዱሳን ከጥቂት ዓመታት
በኋላ እመ ምኔት ትሆኛለሽ ያሉሽን ረሳሽውን? ያ ጊዜ እነሆ ዛሬ
ደረሰ›› ብሎ ነገራትና አባ ይስሐቅ የሚባል መነኩሴ ላከላትና
የእሷ ልጆች ሊሆኑ ከመጡ 600 መነኮሳት ጋር በሦስት ወር
ውስጥ የቅዱስ ሚካኤልን ቤተክርስቲያን ሠርታለች፡፡ ብዙ
ተከታይ መነኮሳትንም አፍርታለች፡፡ በዚህችም ጓንጉት ደሴት
ቆማ ስትጸልይ እንደሁልጊዜው ጌታችን ተገልጦላት ሳለ
‹‹አዳምንና በአርአያህና በአምሳልህ ለምን ፈጠርከው?
በእንጨት መስቀልስ ላይ ለምን ተሰቀልክ? ስለ አዳምና ስለ
ልጆቹ አይደለምን?›› አለቸው፡፡ ጌታችንም ‹‹አዎ ስለ አዳምና
ልጆቹ ስል ነው የተሰቀልሁት›› አላት፡፡ እርሷም ‹‹እንግዲያውስ
መሰቀልህ ስለ እነርሱ ከሆነ ከአቤል ጀምሮ እስከዛሬ የሞቱትን
ከዛሬም በኋላ እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ የሚሞቱትን
ማራቸው፣ ይቅርም በላቸው›› አለችው፡፡ ጌታችንም ‹‹ወዳጄ
ክርስቶስ ሠምራ ሆይ! እስቲ አንቺ ራስሽ ፈረጂ›› በማለት
በጲላጦስ ዘመን አይሁድ ያደረሱበትን እጅግ አሠቃቂ
መከራዎችና የሞቱን ሁኔታ ሁሉ በዝርዝር ከነገራት በኋላ
‹‹እንግዲህ ይህን ውለታ ዘንግተው ከክፋት የማይመለሱትን፣
ለተንኮል የማያርፉትን ልምራቸው ወይስ ልኮንናቸው ይገባል?
እስቲ ፍረጂ›› አላት፡፡ እንደልብ ጓደኛም ብዙ ከተወያዩ በኋላ
መጨረሻ ላይ ቅድስት እናታችን ‹‹አቤቱ ፈጣሪዬ ፈቃድህስ
ቢሆን የአዳም ልጆች ከሥቃይ ከኩነኔ ይድኑ ዘንድ ዲያብሎስን
ይቅር ትለውና ትምረው ዘንድ እለምንሃለሁ፣ የኃጥእን
መመለሱን እንጂ ጥፋቱን አትወድምና፡፡ የምለምንህ ወድጄው
አይደለም ነገር ግን እርሱ ከተማረ በአዳም ልጆች ላይ ሥቃይና
ኩነኔ ሊኖር አይችልም ብዬ በመገመት ነው እንጂ›› አለችው፡፡
ይህንንም ባለችው ጊዜ ጌታችን በጥያቄዋ ተገርሞ ‹‹ሌሎች
ካንቺ በፊት የነበሩ ካንቺም በኋላ የሚነሡ የማያስቡትን እጅግ
የሚያስደንቅ ልመና ለመንሽኝ›› ብሎ ካደነቃት በኋላ ቅዱስ
ሚካኤልን ጠርቶ ‹‹ሳጥናኤል እሺ ካላት ታወጣው ዘንድ ወደ
ሲኦል ይዘሃት ሂድ›› ብሎ አዞታል፡፡ በእዚያም እንደደረሰች
ለዲያቢሎስ ልታስታርቀው እንደመጣች ነገረችው፣ እርሱ ግን
እንኳን ሊመለስላት ይቅርና እርሷንም እጇን ይዞ ወደ ሲኦል
ወረወራት፡፡ በዚህ ጊዜ ይጠብቃት የነበረው መልአክ በእሳት
ሰይፉ ዲያብሎስን በመቅጣት እርሷን መዞ ሲያወጣት በዚህ ጊዜ
በቅዱስ ሚካኤልና በእርሷም ክንፍ ተጣብቀው ዐሥር ሺህ
ነፍሳት ሊወጡ ችለዋል፡፡ ይኸውም የሆነው በዚህች በዛሬይቱ
ዕለት ግንቦት 12 ቀን ነው፡፡ እርሷም በዚህ እጅግ ተደስታ ወደ
ፈጣሪዋ ሄዳ ‹‹አቤቱ ፍርድህ የቀና ምሕረትህ የበዛ ነው››
እያለች ለጌትነቱ ክብር ሰግዳለች፡፡ የእናታችን የቅድስት
ክርስቶስ ሠምራ ረድኤት በረከቷ ይደርብን፣ በጸሎቷ ይማረን፡፡
+ + + + + + + + + + + + + + +
የኢትዮጵያ ብርሃኗ ሐዲስ ሐዋርያ አቡነ ተክለ ሃይማኖት
ፍልሠተ ዐፅማቸው ስለመከናወኑ፡- አቡነ ተክለ ሃይማኖት ከብዙ
ሐዋርያዊ አገልግሎታቸው በኋላ ተዘዋውረው ወንጌልን
ለመስበክ የማይችሉት ዕድሜ ላይ ደረሱ፡፡ በዚህም ጊዜ
‹‹ለሌሎች አበራሁ ለራሴ ግን ጨለምኩ፣ ዓለም አጣፈጥሁ እኔ
ግን አልጫ ሆንኩ…›› ብለው በዓት አጽንተው ከቆሙ
ሳይቀመጡ፣ ከዘረጉ ሳያጥፉ ለ7 ዓመት ቆመው ጸለዩ፡፡
ከ1267-1289 ዓ.ም ባለው ጊዜ ደግሞ በደብረ ሊባኖስ
ካለችው ገዳመ አስቦ ዋሻ በመግባት 8 ጦሮችን ተክለው
እጆቻቸውን በትእምርተ መስቀል በመዘርጋት የክርስቶስን
ሕማምና ሞት፣ ነገረ መስቀልን በማሰብ በተመስጦ ሌትና ቀን
ያለማቋረጥ በጾምና በጸሎት በአርምሞ ተወስነው ሲጋደሉ
ከቁመት ብዛት የተነሣ ጥር 4 ቀን 1289 ዓ.ም. አንዲቱ
የእግራቸው አገዳ ተሰብራለች፡፡ ቅዱስ አባታችን በመዓልትና
በሌሊት በትጋትና በቁመት በተጋድሎ ብዛት አንዲት የአገዳ
እግራቸው ስትሰበር ዕድሜያቸው 92 ዓመት ሆኗቸው ነበር፡፡
ከ1289-1296 ዓ.ም ለሰባት ዓመታት በአንድ እግራቸው
በመቆም ያለምግብና ያለውኃ በትኅርምት ሌትና ቀን እንቅልፍ
በማጣት እንደ ምሰሶ ጸንተው፤ በተመስጦ በትጋት ለሰው ዘር
ሁሉ ድኅነትን ሲለምኑ ኖረዋል፡፡ ከሰባቱ ዓመታት ውስጥ ጥቂት
ውኃ የቀመሱት በአራተኛው ዓመት ብቻ ነበር፡፡ በዚህ ጊዜ
ውስጥ ጌታችን ተገልጦላቸው በሰው አእምሮ ሊታሰብና ሊለካ
የማይችል ትልቅና ልዩ የመንግሥት አዳራሽ ከሰጣቸው በኋላ
የመለኮትን ነገር የሚናገር የእሳት አንደበት ያላቸው
የመንግሥት ልብስ አለበሳቸው፡፡ በመስቀል ምልክት የተጌጡት
ሰባት የሕይወት አክሊላትን አቀዳጅቷቸዋል፡፡ ይኸውም ‹‹ስለ
ቀናች ሃይማኖትህ፣ ሃይማኖትን ለማስተማር መላዋን
ኢትዮጵያን ስለመዞርህ፣ ከአረማውያን ሕዝብ ጋር በሃይማኖት
ስትታገል ደምህን ስለማፍሰስህ፣ ወደ ኢየሩሳሌም ወርደህ ልዩ
ልዩ የቅዱሳን ቦታዎች ስለመሳለምህ፣ በሰባት ዓመታት ቊመት
የአንዱ አገዳ እግርህ ስለመሰበሩ፣ ስለብዙ ጾም ጸሎት
ስግደትህ፣ ስለልብህ ንጽሕናና ቅድስና›› በማለት የሕይወት
አክሊላትን ካቀዳጃቸው በኋላ ዝክራቸውን በማዘከር
መታሰቢያቸውን የሚያደርጉ ሁሉ በዚህ ዓለምም ሆነ
በወዲያኛው ዓለም ፍጹም ዋጋና ፍጹም ክብር እንደሚሰጣቸው
ጌታችን ታላቅ ቃል ኪዳን ገብቶላቸዋል፡፡ ሥጋቸውም ወዴት
ይቀበር ዘንድ እንዳላቸው ሲነግራቸው ‹‹እስከ 57 ዓመት
ሥጋህ ከዚህ ይቀበራል፤ ከ57 ዓመት በኋላ ግን ይህች ዋሻ
ትናዳላች፤ በዚህም ገዳም አደባባይ በስምህ ታላቅ ቤተ
ክርስቲያን ልጆችህ ሠርተው ሥጋህን አፍልሰው በውስጡ
ያኖራሉ›› አላቸው፡፡
ቅዱስ አባታችን በሞት ከማረፋቸው በፊት አስቀድሞ ጌታችን
እንደነገራቸው ሥጋቸው ከነፍሳቸው ከተለየች ከ57 ዓመት በኋላ
የካቲት 19 በጸሎት ላይ ለነበሩት ለአቡነ ሕዝቅያስ
ተገልጠውላቸው ‹‹ጌታ የገባልኝ ቃል ይፈጸም ዘንድ ሥጋዬ
የሚፈልስበት ደረሰ፣ ቀኒቱንም በምስጋናና በጸሎት መንፈሳዊ
በዓል አድርጉ፤ እኔ ኃጥኡ በሞትኩበት ቀን እንደነበረው ምስጋና
አቅርቡ፡፡ ሄደህ ለ12 መምህራንና ለልጆቼ ግንቦት 12
እንዲያከብሩ ንገራቸው፡፡ በፍልሰቴ ቀን አባቴ አባቴ የሚለኝ
ሁሉ ይምጣ ያኔ እኔ ወዳጄ ሚካኤልና ልጄ ፊልጶስ አብረን
መጥተን እንባርካለን፡፡ ምልክት ይሆንህም ዘንድ በምመጣበት
ጊዜ የጠፋው የመቅረዙ መብራት ይበራል›› አሉት፡፡ ከዚህም
በኋላ አቡነ ሕዝቅያስ በአባታችን ተባርከው ሄደው በአራቱም
አቅጣጫ ላሉት 12 መምህራንና ለክርስትያኖች ሁሉ አባታችን
የነገሩትን የፍልሰታቸው በዓል ስለማድረግ ወደ ፍልሰቱ በዓል
ያልመጣም በዚያች ቀን (በሰማይ ለምልጃ) አባቴ እንዳይለው
እርሱም ልጄ እንዳይለው ጨምሮ መልእክቱን ላከላቸው፡፡
እነርሱም ከያሉበት ተሰብስበው መጥተው የቅዱስ አባታችንን
ሥጋቸውን አውጥተው ወደ ቤተ ክርስቲያን አፍልሰው 3 ጊዜ
መቅደሱን አዙረው በዓሉንም አባታችን እንዳሉት በዝማሬና
በምስጋና አክብረው ወደ ውስጥ አስገቡት፡፡ በዚህም ጊዜ ብፁዕ
አባታችን ተክለ ሃይማኖት አስቀድመው እንደተናገሩት ጠፍቶ
የነበረው መብራት ቦግ ብሎ በራ፡፡ ከቅዱስ ሚካኤልና
ከልጃቸው ከአቡነ ፊልጶስ ጋር በመሆንም በዓሉን ያከብር
የነበረውን የተክለ ሃይማኖት የጸጋ ልጆቻቸውን ሁሉም ይባርኩ
ነበር፡፡ የአቡነ ተክለ ሃይማኖት ረድኤት በረከታቸው ይደርብን
በጸሎታቸው ይማረን፡፡

Wednesday, May 18, 2016

=>+*"+<+>+ታላቁ ሊቅ ቅዱስ ያሬድ +<+>+"*+

=>+"+ እንኩዋን ለታላቁ ሊቅ "ቅዱስ ያሬድ" ዓመታዊ
የዕረፍት (የመሰወር) በዓል በሰላም አደረሳችሁ +"+
+*"+ ታላቁ ሊቅ ቅዱስ ያሬድ +"*+
=>ቅዱስ ያሬድ:- ከእግዚአብሔር ያገኘነው አባታችን :
ክብራችን : ሞገሳችን ነውና በምን እንመስለዋለን?
*አንደበቱ ጣፋጭ (ጥዑም)::
*ልቡናው የቅድስና ማሕደር::
*ሕሊናው የምሥጢራት ሠረገላ ነው::
*እስከ አርያም ተነጥቆ የማይፈጸም ምሥጢርን የተመገበ
ማን እንደርሱ!
+ሊቀ ሊቃውንት እዝራ ሐዲስ እንደሚሉት:- "ቅዱስ ያሬድ
ለኢትዮዽያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከራስ ጸጉሯ
እስከ እግር ጥፍሯ : ሙሉ አካሏ ነው::"
<< የሊቁ ዜና ሕይወት በጥቂቱ >>
=>ቅዱስ ያሬድ የተወለደው በ505 ዓ/ም አክሱም አካባቢ
ሲሆን እናቱ ክርስቲና (ታኡክልያ) አባቱ ደግሞ ይስሐቅ
(አብድዩ) ይባላሉ:: ሊቁ በሕጻንነቱ ምሥጢር (ትምሕርት)
አልገባው ብሎ ይቸገር ነበር:: ትምሕርት እንቢ ያለው ሰነፍ ስለ
ነበር አይደለም:: በጥበበ እግዚአብሔር እንጂ::
+ምን ትምሕርት ባይገባው ጾምና ጸሎትን ያዘወትር ነበር::
ልቡናው ደግሞ በእመቤታችንና በልጇ ፍቅር የታሠረ ነበር::
አንድ ቀን ግን መምሕሩ የነገሩት ቀለም አልያዝሕ አለው::
ሲፈትኑትም ባለመመለሱ ተገረፈ::
+ዱላው በጣም ስለ ተሰማው ቅዱሱ ከመምሕሩ ኮብልሎ ማይ
ኪራሕ አካባቢ ሲደርስ ደክሞት አርፎ እግዚአብሔር ትጋትንና
ተስፋ አለመቁረጥን ከትል አስተማረው:: ትሏ 6 ጊዜ ወድቃ
በ7ኛው ፍሬዋን ስትበላት ተመልክቷልና::
+ከዚህ በሁዋላ ቅዱስ ያሬድ ወደ መምሕሩ ተመልሶ : ይቅርታ
ጠይቆ ትምሕርት ጀመረ:: ሊቁም ትጋትንና ጸሎትን ከሰጊድ
ጋር አበዛ:: እግዚአብሔር ደግሞ በድንግል እናቱ አማካኝነት
የምሥጢር ጽዋን አጠጣው::
+ካህኑ ያሬድ እንዲያ አልገባህ ያለው ምስጢር ተገልጦለት
በጥቂት ጊዜ ብሉይ ከሐዲስ ወሰነ:: በምሥጢር ባሕርም ይዋኝ
ጀመር::
+ያን ጊዜ ሰማያዊ ዜማ አልተገለጠም ነበርና በጸሎት ላይ ሳለ
ተደሞ መጣበት:: 3 መላእክት በ3 ወፎች አምሳል መጥተው
አነጋገሩት:: ድንገትም ነጥቀው ወደ ሰማያት : ወደ ልዑላኑ
መላእክት ዘንድ አደረሱት:: ሊቁ በሰማያት ልዩ ምሥጢር : ልዩ
ምስጋናና ልዩ ዜማን አዳመጠ:: ይሕንን ምስጋና ብዙ ቅዱሳን
ቢሰሙትም ቅዱስ ያሬድ ግን ይዞት እንዲወርድ ተፈቀደለት::
+ሊቁ ወደ ምድር ተመልሶ በታላቅ ተመስጦ አክሱም ጽዮን
ውስጥ በሃሌታ አመሰገነ:: ሕዝቡና ንጉሡም ከጣዕሙ የተነሳ
አደነቁ:: ቅዱስ ያሬድ ለተወሰነ ጊዜ በአክሱምና ደብረ ዳሞ
ሲያገለግል ቆይቶ : ከመሬት ክንድ ከስንዝር ከፍ ብሎ
ለእመቤታችን አንቀጸ ብርሃንን ደርሶላት ከሃገሩ ወጣ::
+ቅዱስ ያሬድ በቀሪ የሕይወቱ ዘመናት:-
1."5" ያሕል መጻሕፍትን ጽፏል::
2.በጣና ቂርቆስ : በዙር አባና በሌሎችም ቦታዎች ወንበር
ዘርግቶ ብዙ ደቀ መዛሙርትን አፍርቷል::
3.በሰሜን ተራሮች አካባቢ በትጋሃ መላእክትና በተባሕትዎ
ኑሯል::
+በ576 (571) ዓ/ም በተወለደ በ71 ዓመቱ በዚህች ቀን
ተሰውሯል::
=>አባቶቻችን:-
*ጥዑመ ልሳን
*ንሕብ
*ሊቀ ሊቃውንት
*የሱራፌል አምሳያ
*የቤተ ክርስቲያን እንዚራ
*ካህነ ስብሐት
*መዘምር ዘበድርሳን
*ማኅሌታይ
*ልዑለ ስብከት
እያሉ ይጠሩታል::
=>የቅዱሱ ጸሎትና በረከት ሃገራችንን ከክፉው ሁሉ
ይጠብቅልን::
=>ግንቦት 11 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=
1.ቅዱስ ያሬድ ካህን ወማኅሌታይ
2.አቡነ ሐራ ድንግል ጻድቅ
3.ክርስቲናና ይስሐቅ (የቅዱስ ያሬድ ወላጆች)
4.ቅድስት ታውክልያ እናታችን (ንግሥናን ንቃ ሰማዕት የሆነች)
5.ቅድስት ኤፎምያ ሰማዕት
6.ቅድስት ሶፍያ ሰማዕት
7.ቅድስት አናሲማ ገዳማዊት
8.አባ በፍኑትዮስ ገዳማዊ
9.አባ አሴር ሰማዕት (ኢትዮዽያዊ)
10.አባ በኪሞስ ጻድቅ
=>ወርሐዊ በዓላት
1.ቅዱስ ገላውዴዎስ ሰማዕት
2.ቅዱስ ፋሲለደስ ሰማዕት
3.ብፁዐን ኢያቄም እና ሐና
=>+"+ እንዲህ ያለው ሰው ከአሥራ አራት ዓመት በፊት እስከ
ሦስተኛው ሰማይ ድረስ ተነጠቀ:: እንዲህ ያለውንም ሰው
አውቃለሁ:: በሥጋ እንደ ሆነ ወይም ያለ ሥጋ እንደሆነ
አላውቅም:: እግዚአብሔር ያውቃል:: ወደ ገነት ተነጠቀ::
ሰውም ሊናገር የማይገባውን: የማይነገረውን ቃል ሰማ:: +"+
(2ቆሮ. 12:2-5)
<ወስብሐት ለእግዚአብሔር>

Monday, May 16, 2016

=>+*"+<+>+ግንቦት 9+<+>+"*+

አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
አሜን
#ግንቦት 9
#የታላቁ_ጻድቅ_ንጉሥ_የቆ ስጠንጢኖስ_እናት
#የከበረች_ንግሥት_እሌኒ_ ዐረፈች፡፡ ጌታችን የተሰቀለበት
መስቀል ሙት እያስነሳ ድውይ እየፈወሰ አጋንንት እያወጣ
የተለያዩ ገቢረ ተአምራት ሲሰራ ክፉዎች አይሁዶች አይተው
ሕዝቡ ክርስቲያን እንዳይሆኑ በመፍራት በ34 ዓ.ም
ከኢየሩሳሌም ወጣ ብሎ በሚገኝ ቦታ ቆፍረው ቀበሩት፡፡
ከዚያም የከተማውን ቆሻሻ ሁሉ ከዚያ መስቀሉ በተቀበረበት
ቦታ ላይ እየደፉ ከዘመን ብዛት ቦታው በቆሻሻ ክምር የተነሣ
ተራራ ሆነ፡፡ እስራኤልን ከሮም ቅኝ አገዛዝ ነጻ ለማውጣት
ከ66-70 ዓ.ም ባደረጉት እንቅስቃሴ ጥጦስ የተባለው የሮም
ንጉሠ ነገሥት ዘምቶ ኢየሩሳሌምን በ70 ዓ.ም ደመሰሳት፡፡
ትልቁን የአይሁድ ቤተመቅደስንም አቃጠለው፡፡
እስራኤላውያንም በመላው ዓለም ተበተኑ፡፡ ከዘመነ ሐዋርያት
ጀምሮ በተከታታይ በሮም የነገሡ ነገሥታት /ቄሳሮች/
በክርስቲያኖች ላይ የማያባራ መከራ አድርሰዋል፡፡ ክርስቲያኖች
የተቀበረውን መስቀል አስፈልገው ለማውጣት ቀርቶ
ሃይማኖታቸውን የማመን ነጻነት ስላልነበራቸው ቅዱስ
መስቀል ለ300 ዓመታት ያህል ተቀብሮ የጉድፍ መጣያ ሆኖ
ቆየ፡፡ የመስቀሉ የመገኘት ታሪክ የቤተክርስቲያን የመከራ
ዘመን አልፎ የዕረፍትና የሰላም ዘመን ሲመጣ ለብዙ ዘመን
ተቀብሮ የተረሳውን መስቀል ባለቤቱ መድኃኔዓለም
አልረሳምና እርሱ የፈቀዳት ዕለት ስትደርስ በዕሌኒ ንግሥት
አማካኝነት ከተቀበረበት እንዲወጣ አደረገ፡፡
ዕሌኒና ተርቢኖስ የሚባሉ ሁለት ደጋግ ክርስቲያኖች ተጋብተው
ይኖሩ ነበር፡፡ ተርቢኖስና ዕሌኒ ኑሮአቸው ፍቅርና ሰላም
የሰፈነበት በመሆኑ ለብዙ ሰዎች እንደ ምሳሌ ሆነው ይኖሩ
ነበር፡፡ ተርቢኖስ ነጋዴ ነበር፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን ራቅ ወዳለ
ሀገር በመርከብ ለንግድ ሄደ፡፡ ዕሌኒም ባለቤቷ ተርቢኖስ
ለንግድ ወጥቶ እስኪመለስ ስለባሏ ከመጸለይና ከማሰብ በቀር
ከግቢዋ አትወጣም ነበር፡፡ አንድ ጊዜ ተርቢኖስ ለንግድ ሄዶ
ብዙ ዓመታትን ቆይቶ ከጓደኞቹ ጋር ወደሀገሩ ሲመለስ
ከነጋዴዎች አንዱ "በእግዚአብሔር ፈቃድ ከሽፍታና ከማዕበል
ከልዩ ልዩ አደጋ ተርፈን በሰላም ተመልሰን ሚስቶቻችን ሌላ
ሳይወዱ ሳይለምዱ እናገኛቸው ይሆን?" ብሎ ጠየቀ፡፡ ተርቢኖስ
ግን "እንኳን በሰላም አደረሰን እንጂ ሚስቴን በዚህ
አልጠረጥራትም" ብሎ ሲመልስ ሌላው ጓደኛው "ያንተ ሚስት
ከማን ትበልጣለችና ነው አሁን ሄጄ ከሚስትህ ጋር ለምዳኝ
ወዳኝ ወድጃት ብመጣስ ምን ትቀጣለህ?" አለው፡፡
ተርቢኖስም በሚስቱ ዕሌኒ ተማምኖ "ይህንን ብታደርግ ይህን
ያህል ዓመት የለፋሁበት ሀብት ከነትርፉ ውሰድ አንተም
ብታደርግ እንዲሁ ሀብትህ ከነትርፉ ለእኔ ይሁን" ተባብለው
ተወራረዱ፡፡
ከዚያም መርከቡ ወደብ ከመድረሱ በፊት ነጋዴው ወደ ዕሌኒ
ቤት ደረሰና በሩን አንኳኩቶ ሠራተኛይቱን "ዕሌኒን ማነጋገር
እፈልጋለሁና ንገሪልኝ" ብሎ ጠየቃት፡፡ እርሷም እያፈረች
የተላከችውን ለዕሌኒ ነገረቻት፡፡ ዕሌኒም ተቆጥታ "ከመች
ወዲህ ነው እንግዳ የማነጋግረው?" ብላ አሳፈረቻት፡፡
ሠራተኛይቱም ለነጋዴው መልሱን ስትነግረው ነጋዴው
እንደማይሆንለት ከተረዳ በኋላ ሌላ ተንኮል አቀደና
ለሠራተኛይቱ "ባልና ሚስቱ ብቻ የሚያውቁትን አንድ ነገር ብቻ
ብትሰጪኝ ብዙ ገንዘብና ወርቅ እሰጥሻለሁ" ብሎ ወርቅ
ሰጣት፡፡ ሠራተኛይቱም "ሁለቱ ብቻ የሚያውቁት የእመቤቴ
ሀብል አለ ያንን እመጣልሀለሁ መጀመርያ አንተ በከተማው
ውስጥ እየዞርህ ነጋዴዎችን መጡ የብስ ረገጡ እያልክ አስወራ
ከዚያም ተመልሰህ እንድትመጣ" ብላ ሰደደችው፡፡ ነጋዴውም
እንደተመከረው የነጋዴዎቹን መምጣት በከተማይቱ እንዳወራ
የነጋዴዎቹ ቤተሰቦች ነጋዴዎችን ለመቀበል ዝግጅት ማድረግ
ጀመሩ፡፡ የዕሌኒም ሠራተኛ "እመቤቴ ነጋዴዎች መጡ ተብሎ
ይወራልና፡፡ ባለቤትዎ በሰላም ስለመጡ ይዘገጃጁ ገላዎን
ይታጠቡ" ብላ መከረቻት፡፡ ዕሌኒም ገላዋን ስትታጠብ ያንገቷን
ሐብል ቁጭ ካደረገችበት ቦታ ሠራተኛይቱ አንስታ ለነጋዴው
በተቃጠሩበት ዕለት ሰጠችው፡፡ ነጋዴውም ለሠራተኛይቱ
የውለታዋን ብዙ ገንዘብና ወርቅ ሰጥቶአት ደስ እያለው ወደ
ጓደኞቹ ሄደ፡፡ ለተርቢኖስ "ሚስትህን ለምጃት ወድጃት
መጣሁ" አለው፡፡ ተርቢኖስም "ውሸት ነው ለዚህ ምን ምልክት
አለህ?" ብሎ ጠየቀው፡፡ ተንኮለኛውም ነጋዴ ያንን ሐብል
አውጥቶ "ይህ ሀብል የሚስትህ አይደለምን?" ብሎ ሰጠው፡፡
ተርቢኖስም ደነገጠ የሚናገረውን አጣ፡፡ በውርርዱም መሠረት
ሀብቱን ሁሉ አስረከበና ባዶ እጁን ወደቤቱ እያዘነ እየተቆጨ
ሔደ፡፡
ባለቤቷን በናፍቆትና በታማኝነት ስትጠብቅ የከረመችው ዕሌኒ
በተርቢኖስ ያልተለመደ ሀዘንና ብስጭት ግራ ተጋብታ
"ወንድሜ ምን ሆነሀል? ለወትሮው እንኳን ይህን ያህል ዘመን
ተለያይተን ቀርቶ ለጥቂት ቀናት ተለያይተን እንኳ ለጥቂት
ቀናት ተለያይተን ስንገናኝ እንነፋፈቃለን፡፡ አሁን ግን
ከመጣህበት ጊዜ ጀምሮ አዝነህ አይሃለሁ" ብላ ጠየቀችው፡፡
ተርቢኖስም "ብዙ የደከምኩበትና የለፋሁበት ሀብት ንብረቴ
እንዳለ ማዕበል አጠፋብኝ እኔ ያላዘንኩ ማን ይዘን?" አላት፡፡
ዕሌኒም የተማረች ናትና "እግዚአብሔር ሰጠ እግዚአብሔር ነሣ
የእግዚአብሔር ስም የተመሰገነ ይሁን እንዳለ ኢዮብን
አስበው፡፡ አንተ እንኳን በሰላም መጣህ እንጂ ሀብቱ ውሎ
አድሮ ይመጣል..." እያለች አጽናናችው፡፡ ተርቢኖስም "እንግዲህ
በተከበርኩበት ሀገር ተዋርጄ፣ በሰጠሁበት ሀገር ለምኜ ለመኖር
አልችልምና ወደሌላ ወደማያውቁኝ ሀገር እሔዳለሁ አንቺ ግን
ሁሉ ይወድሻል ያከብርሻል ከወደድሸው ጋር ኑሪ" አላት፡፡
ዕሌኒም "በደስታ ጊዜ አብሬህ እንደሆንኩ በችግርም ጊዜ
ልለይህም የእኔንና ያንተን አንድነት ችግር አይፈታውም ከአንተ
ተለይቼ ወዴት እቀራለሁ ወደምትሄድበት አብሬህ እሄዳለሁ"
ብላ ተነሳች፡፡ ሁለቱም ቤታቸውን ጥለው ሲሄዱ በመንገድ ላይ
ተርቢኖስ በልቡናው ይዞት የነበረውን ምሥጢር አወጣው
"ዕሌኒ ስወድሽ የጠላሽኝ ሳምንሽ የከዳሽኝ ምን አድርጌሽ
ነው?" ብሎ ጠየቃት፡፡ ዕሌኒም "እኔ አንተን አልጠላሁም
አልከዳሁምም ይህንን ሐሳብ እንዴት አሰብህ?" ብትለው ከኪሱ
አውጥቶ ሀብሉን አሳያትና የሆነውን ሁሉ ነገራት፡፡ ዕሌኒም
ያልጠበቀችው ነገር ስለተፈጸመ አዝና የሆነውን እውነተኛ ታሪክ
በሙሉ ነገረችው፡፡ ተርቢኖስ ግን አላመናትም፡፡ ከባህር ዳር
በደረሱ ጊዜ በቁመቷ ልክ ሣጥን አሠርቶ ዕሌኒን በውስጡ
አስገባትና "ብታደርጊውም ባታደርጊውም እንደሥራሽ ሥራሽ
ያውጣሽ" ብሎ ወደ ባሕሩ ወረወራት፡፡
ዕሌኒ ያለችበት ሣጥን በፈቃደ እግዚአብሔር እየተንሳፈፈ
ከወደብ ደረሰ፡፡ በዚያ ወደብ አካባቢ ምዕራብ ሮምን ያስተዳደር
የነበረው ኮስታንዲዮስ (ቁንስጣ) የተባለው ንጉሥ ነበርና
ሣጥኑን አይቶ አውጥቶ እንዲከፍቱት ወታደሮችን አዘዘ፡፡
ሣጥኑን አውጥተውም ሲከፍቱት እጅግ የተዋበች ሴት ሆና
አገኟት፡፡ ንጉሡም ዕሌኒን ወስዶ ሚስቱ አደረጋት፡፡
ኮስታንዲዮስ (ቁንስጣ) የመክስምያኖስ ቄሳር ሆኖ ምዕራብ
ሮምን ያስተዳደር ነበር፡፡ ንግስት ዕሌኒም በ272 ዓ.ም ታላቁ
ቆስጠንጢኖስን ወለደችለት ቆስጠንጢኖስም ገና በወጣትነቱ
የአባቱ እንደራሴ ሆኖ እንደሠራ አባቱ ሞተ፡፡ የአባቱ
ባለሟሎችና ሕዝቡ ተስማምተው የ18 ዓመቱን
ቆስጠንጢኖስን በአባቱ ቦታ ሐምሌ 25 ቀን 316 ዓ.ም
በሮም ምዕራብ ክፍል በገላትያ አነገሡት፡፡ በጦር ሜዳዎች
ብዙ የጀግንነት ሥራዎች ስለሠራ በሠራዊቱ ዘንድ ይወደድ
ነበር፡፡ ሊቀ ነቢያት ሙሴን ወላጅ እናቱ በፈርዖን ቤት
ሃይማኖቱን ባሕሉን ታሪኩን በሚገባ እያስተማረች
እንዳሳደገችው ሁሉ ንግሥት ዕሌኒም ልጇን ቆስጠንጢኖስን
ከልጅነቱ ጀምሮ ስለክርስትና ሃይማኖትና ስለክርስቲያኖች
መከራ ታስተምረው ስለነበር በክርስቲያኖች ላይ የነበረው
አመለካከት በሮም ከነገሡት ቄሣሮች ሁሉ የተሻለ ነበር፡፡
በተለይም በ312 ዓ.ም ከጠላቱ ከመክስምያኖስ ጋር ለመዋጋት
"ምታ ነጋሪት ክተት ሠራዊት" ብሎ ለዘመቻ እንደተሰለፈ
በራእይ በሰማይ ላይ "በዚህ መስቀል (ምልክት) ጠላትህን ድል
ታደርጋለህ" የሚል የመስቀል ቅርጽና የተጻፈ ጽሑፍ ስላየ
ለሠራዊቱ የመስቀል ምልክት በመሳሪያቸውና በሰንደቅ
ዓላማው ላይ እንዲያደርጉ አዘዘ፡፡ ወደያው ጦርነት ቢገጥም
ጠላቱን ድል ነሥቶ በጠቅላላው የሮም መንግሥት ግዛቶች ሁሉ
ገዥ ሆነ፡፡
ታላቁ ቆስጠንጢኖስ የሮም ንጉሠ ነገሥት ከሆነ በኋላ በ300
ዓመታት ውስጥ ለመጀመርያ ጊዜ ለክርስቲያኖች የነጻነት ዐዋጅ
ዐወጀ፡፡ ክርስትናም ብሔራዊ ሃይማኖት ተባለች፡፡ ንግሥት
እሌኒም በተፈጠረላት አመች ሁኔታ በመጠቀም የጌታችን
መስቀል ከተቀበረበት ለማውጣት በ327 ዓ.ም
ወደኢየሩሳሌም ሔደች፡፡ ዕሌኒ ልጅዋ ቆስጠንጢኖስ
ክርስቲያን ከሆነላት ወደ ኢየሩሳሌም ሔዳ መስቀሉን
ለመፈለግ እንዲሁም በኢየሩሳሌም ያሉ ቅዱሳት መካናትንና
አብያተ ክርስቲያናትን ለማሳነጽ ለእግዚአብሔር ተሳለች፡፡ ከዚህ
በኋላ ቆስጠንጢኖስ አምኖ በ337 ዓ.ም ተጠመቀ፡፡ ቅድስት
ዕሌኒም ወደ ኢየሩሳሌም ሔደች፡፡ ከእርሷም ጋር ብዙ
ሠራዊት ነበር፡፡ እንደደረሰችም ስለ ቅዱስ መስቀል
መረመረች፡፡ ነገር ግን ቦታውን የሚያስረዳት አላገኘችም፡፡
የአይሁድ ወገን እንቢ ቢሉም በኋላ ግን ባደረገችው ጥረት
አረጋዊው ኪራኮስ የጎልጎታን ኮረብታ አመለከታትና አስቆፍሪው
ብሎ ነገራት ኪራኮስም ዘመኑ ከመርዘሙ ጋር ተያይዞ
እውነተኛው ተራራ ይህ ነው ብሎ ማሳየት ባለመቻሉ "ከሦስቱ
ተራሮች አንዱ ነው" ስላላት አይሁድ ተራሮቹን ይቆፍሩ ዘንድ
አዘዘቻቸው፡፡ የጌታችን ቅዱስ መስቀል በሚያደርጋቸው
አስደናቂ ተአምራት የተነሣ ሕዝቡ እያመነ በተቸገሩ ግዜ
ክፉዎች አይሁዶች ማንም እንዳያገኘው የኢየሩሳሌም ነዋሪ
ሁሉ የእቤቱን ቆሻሻ የከበረ መስቀል ባለበት ቦታ እንዲጥል
አዘው ስለነበር ከሁለት መቶ ሃምሳ ዓመት በላይ ጥራጊ
ስለጣሉበት ታላቅ ተራራ ሆነ፡፡
ዕሌኒ ተራሮቹን ለማስቆፈር ከሦስቱ ተራሮች የቱ እንደሆነ
ለመለየት ደመራ አስደምራ ብዙ ዕጣን በመጨመርና
በማቃጠል ከአኢየሩሳሌም ወጣ ብለው ያሉትን ኮረብቶች
አሳያት፡፡ የዕጣኑ ጢስ ወደ ሰማይ በመውጣት በቀጥታ ተመልሶ
መስቀሉ ባለበት ተራራ ላይ በማረፍና በመስገድ መስቀሉ
ያለበትን ትክክለኛ ሥፍራ አመለከታት፡፡ ቅዱስ ያሬድም "ሰገደ
ጢስ" ጢሱ ሰገደ ብሎታል፡፡ ከዚያም መስከረም 16 ቀን
ቁፋሮው እንዲጀመር አዘዘች፡፡ ሰባት ወር ያህል ከተቆፈረ በኋላ
መጋቢት 10 ቀን ሦስት መስቀሎች በአንድነት ተገኙ፡፡ ንግሥት
ዕሌኒም የክብር ባለቤት ጌታችን የተሰቀለበት የትኛው እንደሆነ
ለማወቅ በወደደች ጊዜ "ከራሱ በላይ ይህ የናዝሬቱ ኢየሱስ
የአይሁድ ንጉሥ ነው" የሚል የተቀረጸበት ጽሑፍ ያለው
እንደሆነ የኢየሩሳሌም ኤጲስቆጶስ ቅዱስ መቃርስ ነገራት፡፡
ከእርሱም ምልለክት ታይ ዘንድ ወደደች፡፡ የሞተ ሰው አምጥታ
በሁለቱ መስቀሎች ላይ በተራ ቢታስቀምጠው አልተነሣም፡፡
በመጨረሻ ጽሕፈት ባለው በአንዱ መስቀል ላይ
ቢታስቀምጠው ያንጊዜ የሞተው ሰው ተነሣ፡፡ በዚህም
የጌታችንን መስቀል ለየችው፡፡ ዕሌኒም ለጌታችን መስቀል
ሰገደችለት፡፡ ክርስቲያኖች ሁሉ ሰገዱለት፡፡ በየሀገሩ ያሉ
ክርስትያኖች ሁሉ የመስቀሉን መገኘት በሰሙ ግዜ መብራት
አብርተው ደስታቸውን በመግለጥ ለዓለም እንዲታወቅ
አደረጉ፡፡ በዚህም ምክንያት ይህ ታላቅ የድኅነት ምልክት
የሆነው መስቀል የኢትዮጵያ ቤተክርስትያን ደመራ በመደመር
በታላቅ መንፈሳዊ ሥነ ሥርዓት ታከብረዋለች፡፡
ንግሥት ዕሌኒ መስከረም 16 ቀን 320 ዓ.ም በዕጣን ጢስ
ምልክት ቁፋሮ አስጀምራ መጋቢት 10 ቀን አግኝታ
በማውጣት ታላቅ ቤተ መቅደስ ጎልጎታ ላይ ሠርታ በክብር
አስቀመጠችው፡፡ ጌታችን ስለ ቅዱስ መስቀሉ ለቅድስት
ንግስት ዕሌኒ ቃልኪዳን ሲገባላት እንዲህ አላት፡- ‹‹በደሜ
የከበረ የመስቀሌን ስም የሚጠራውን እርሱን እምረዋለሁ፡፡
በዕፀ መስቀሌ ቤ/ክ ውስጥ የለመነውን የጸለየውን ሰው
መላእክት እንኳን ተድላ ደስታውን ወደማያውቁት ወደ
መንግሥተ ሰማያት አዳራሽ ያለወቀሳ ይገባል፡፡ ለከበረ
መስቀሌ ከቅርብም ከሩቅም ወደ ቤተ ክርስቲያኑ ተጉዞ
የመጣውን ወደ መቃብሬ ኢየሩሳሌም እንደጓዘ እኔ
አደርግለታለሁ፡፡ ይህንንም መጽሐፍ የጻፈ ያጻፈ ወይም
ያነበበውን የተረጎመውን ቃሉን በዕዝነ ልቡና የሰማውን
የመጽሐፉንም ገበታዎቹን የሳመውን በተጸለየበት ውኃም
የተጠመቀውን እኔ በሕይወት መጽሐፍ በዓምደ ወርቅ ላይ
በወርቅ ቀለም ስሙን እጽፈዋለሁ፡፡›› (ድርሳነ መስቀል)
የጌታችንን ቅዱስ መስቀል ንግሥት ዕሌኒ መጋቢት 10 ቀን
አግኝታ በማውጣት ታላቅ ቤተ መቅደስ ጎልጎታ ላይ ሠርታ
በክብር ካስቀመጠችው በኋላ ከዚያ ዕለት ጀምሮ እንደ ፀሐይ
እያበራ ድውይ እየፈወሰ አጋንንት እያባረረ ልዩ ልዩ ገቢረ
ተአምራት እየሠራ ሙት እያነሣ ዕውር እያበራ ተአምራቱን
ቀጠለ፡፡ ይህንንም የሰማው ከኃያላን ነገሥታት መካከል የፋርስ
ንጉሥ መስቀሉን ማርኮ ፋርስ ወስዶ አስቀመጠው፡፡ ነገር ግን
ንጉሡ ሕርቃል የጌታችንን ቅዱስ መስቀል አስመልሶታል፡፡
በዚህ ጊዜ የኢየሩሳሌም ምእመናን የድሉን ዜና ሰምተው
ስለነበር የአንድ ቀን መንገድ ያህል ሄደው በመቀበል ካህናቱ
በዝማሬና በእልልታ ችቦ አብርተው ተቀብለዋቸዋል፡፡
የቤተክርስቲያን አባቶች እንደሚሉት ንጉሡ ሕርቃል ይህንን
ታላቅ ድል ለማግኘትና የጌታን ቅዱስ መስቀል ከአሕዛብ
(ከፋርሶች) እጅ ለማስመለስ የቻለው በዚያን ጊዜ አብያተ
ክርስቲያንናት ሁሉ ለአንድ ሳምንት (አንድ ሱባዔ) ባደረጉት ጾም
ጸሎት ነው፡፡ ይህንንም ለማስታወስና ጌታን ለማመስገን
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንና የግብጽ ኮፕቲክ
ቤተ ክርስቲያን በየዓመቱ የዐቢይ ጾም ከመጀመሩ አስቀድሞ
"ጾመ ሕርቃል" ብለው አንድ ሳምንት ይጾማሉ፡፡ የጌታ
መስቀል ለብዙ ጊዜያት ኢየሩሳሌም ከቆየ በኋላ ነገሥታት
‹‹ይህን መስቀል እኔ ልውሰድ፣ እኔ ልውሰድ›› በማለት ጠብ
ፈጠሩ፡፡ በዚህ ጊዜ የአንጾኪያ፣ የኤፌሶን፣ የአርማንያ፣ የግሪክ፣
የእስክንድርያ፣ የመሳሰሉት የሃይማኖት መሪዎች ጠቡን
አበረዱት፡፡ ከዚያም አያይዘው በኢየሩሳሌም የሚገኘውን
የክርስቶስን መስቀል ከአራት ከፍለው በዕጣ አድርገው
በስምምነት ተካፍለው ከሌሎች ታሪካዊ ንዋያተ ቅዱሳት ጋር
በየሀገራቸው ወስደው በክብር አስቀመጡት፡፡ የቀኝ ክንፉ
የደረሰው ለአፍሪቃ ስለነበር ከታሪካዊ ንዋየ ቅዱሳት ጋር
በግብጽ የሚገኘው የእስክንድርያ ፓትርያርክ ተረክቦ ወስዶ
በክብር አስቀመጠው፡፡ ግማደ መስቀሉ ለብዙ ዘመን
በእስክንድርያ ሲኖር በግብጽ ያሉ እስላሞች እየበዙ ኃይላቸው
እየጠነከረ ሲሔድ በእስክንድርያ የሚኖሩ ክርስትያኖች ላይ
ሥቃይ ያጸኑባቸው ጀመር፡፡ ክርስቲያኖቹም አንድ ሆነው
መክረው ለኢትዮጵያዊው ዓጼ ዳዊት እንዲህ የሚል መልእክት
ላኩ "ንጉሥ ሆይ! በዚህ በግብጽ ያሉ እስላሞች መከራ
አጽንተውብናልና ኃይልህን አንሥተህ አስታግስልን" ብለው
ጠየቁት ዳግማዊ ዐጼ ዳዊትም ለመንፈሳዊ ሃይማኖት
ቀንተው የክርስቶስ ፍቅር አስገድዷቸው 20,000 ሠራዊት
አስከትለው ወደ ግብጽ ዘመቱ በዚህ ጊዜ በግብጽ ያሉ ኃያላን
ፈሩ ተሸበሩ፡፡ ንጉሡ ዳግማዊ ዳዊትም እንዲህ የሚል
መልዕክት ለእስላሞቹ ላከ፡- "በተፈጥሮ ወንድሞቻችሁ ከሆኑት
ክርስቲያኖች ካልታረቃችሁ ሀገራችሁን መጥቼ አጠፋለሁ"
የሚል ማስጠንቀቂያ ላከ፡፡
የንጉሡ መልዕክትም ለእስላሞቹ እንደደረሳቸው ፈርተው እንደ
ጥንቱ በየሃይማታቸው ጸንተው በሰላም እንዲኖሩ ከክርስቲያን
ወንድሞቻቸው ጋር ታረቁ፡፡ መታረቃቸውን ዓጼ ዳዊት ሰሙ
በዚህም ጉዳይ ንጉሡ ደስ አላቸው፡፡ እግዚአብሔርንም
አመሰገኑ በግብጽ የሚኖሩ ክርስቲያኖችም ከ12,000 ወቄት
ወርቅ ጋር ደስታቸውን ለኢትዮጵያዊው ንጉሥ ለዳግማዊ
ዳዊት በደብዳቤ አድርገው ላኩላቸው፡፡ ንጉሡም የደስታውን
ደብዳቤ ተመልክተው ደስ አላቸው ወርቁን ግን መልሰው
በመላክ እንዲህ የሚል ደብዳቤ ጻፉ፡- "በግብጽ የምትኖሩ
የክርስቶስ ተከታዮች ሁሉ እንኳን ደስ አላችሁ የላካችሁልኝ
12,000 ወቄት ወርቅ መልሼ ልኬላችኋለሁ፡፡ የእኔ ዓላማ
ወርቅ ፍለጋ አይደለም የክርስቶስ ፍቅር አስገድዶኝ በተቻለኝ
ችግራችሁን ሁሉ አስወገድኩላችሁ፤አሁንም የምለምናችሁ
በሀገሬ ኢትዮጵያ ረሀብና ቸነፈር ድርቅ ስለወረደብኝ
መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተሰቀለበት ቅዱስ መስቀልና
የቅዱሳን አጽም ከሌሎች ክቡራን ዕቃዎች ጋር እንድትልኩልኝ
ነው" የሚል ነበር፡፡
እስክንድርያ ያሉ ምዕመናንም የዐፄ ዳዊት "በሀገሬ ኢትዮጵያ
ረሀብና ቸነፈር ድርቅ ስለወረደብኝ መድኃኒታችን ኢየሱስ
ክርስቶስ የተሰቀለበት ቅዱስ መስቀልና የቅዱሳን አጽም
ከሌሎች ክቡራን ዕቃዎች ጋር እንድትልኩልኝ" የሚለው
መልዕክት እንደደረሳቸው ከሊቃነ ጳጳሳትና ከኤጲስ ቆጶሳቱ ጋር
ውይይት በማድረግ "ይህ ንጉሥ ታላቅ ክርስቲያን ነው፡፡ ስለዚህ
ልቡን ደስ እንዲለው የፈለገውን የጌታችንን ግማደ መስቀል
ከቅዱሳን ዐፅምና ንዋየ ቅዱሳት ጋር አሁን በመለሰው ወቄት
ወርቅ የብርና የነሐስ የመዳብና የወርቅ ሣጥን አዘጋጅተን
እንላክለት" ብለው ተስማምተው በክብር በሥነ ሥርዓት
በሠረገላና በግመል አስጭነው ስናር ድረስ አምጥተው
ለኢትዮጵያውያን ባስረከቧቸው ጊዜ በእጃቸው እያጨበጨቡ
በእግራቸው እያሸበሸቡ በግንባራቸው እየሰገዱ በክብር በደስታ
ተቀበሏቸው፡፡
ግማደ መስቀሉ ወደ መካከለኛው ኢትዮጵያ ሳይደርስ በድንገት
ዐፄ ዳዊት ስናር በሚባል በረሃ ላይ አረፉ፡፡ ግማደ መስቀሉም
የግድ በዚያው በስናር መቆየት አስፈለገው፡፡ ከዚህ በኋላ የሟቹ
የዳግማዊ ዳዊት ልጅ ዐፄ ዘርዓ ያዕቆብ እንደነገሡ ወደ ስናር
ሔደው ግማደ መስቀሉን ከሌሎቹ ንዋያተ ቅዱሳት ጋር
አምጥተው በመናገሻ ከተማቸው በደብረ ብርሃን ላይ
ቤተመቅደስ ሠርተው ለማስቀመጥ ሲደክሙ በሕልማችው
አንብር መስቀልየ በዲበ መስቀል "ወዳጄ ዘርዐ ያዕቆብ ሆይ
መስቀሌን በመስቀለኛ ቦታ ላይ አስቀምጥ" የሚል ራእይ
አዩ፡፡
ከእስክንድርያ ሀገር ከመስቀሉ ጋር በልዩ ልዩ ሣጥን ተቆልፈው
የመጡትም ዝርዝር ስማቸው ጌታችን በዕለተ ዓርብ ለብሶት
የነበረው ቀይ ልብስ፣ ከሮም የመጣው ከለሜዳው፣ ሐሙት
የጠጣበት ሰፍነግ /ጽዋ/፣ ዮሐንስ የሳለው ኩርዓተ ርዕሱ ስዕል
እንዲሁም የተለያዩ የቅዱሳን አጽም፣ ከግብጽ ታላላቅ ገዳማት
የተቆነጠረ አፈር፣ የዮርዳኖስ ውሃ ይገኛል፡፡ ንጉሡም
መስቀለኛ ቦታ እየፈለጉ በኢትዮጵያ አውራጃዎች ሁሉ
በመፈለግ ከብዙ ቦታ አስቀምጠውት ነበር፡፡ ለምሳሌ በሸዋ
በደብር ቅዱስ ደብረ ጽጌ ማርያም ገዳም፣ በማናገሻ ማርያም፣
በወጨጫ መስቀሉን አሳርፈውት ነበር፡፡ ነገር ግን
የመጨረሻውን ቦታ ባለማግኘታቸው በራዕይ እየደጋገመ
አንብር መስቅልየ በዲበ መስቅል መስቀሌን በመስቀለኛ
ሥፍራ አስቀምጥ እያለ ይነግራቸው ነበር፡፡ ዓጼ ዘርዓ
ያዕቆብም ለሰባት ቀን ሱባዔ ገቡ፡፡ በዚያም የተገለጸላቸው
"መስቀለኛውን ቦታ የሚመራህ ዓምደብርሃን ይመጣል"
አላቸው፡፡ እርሳቸውም ከዚያ እንደወጡ መስቀለኛውን ቦታ
የሚመራ የብርሃን ዓምድ ከፊታቸው መጥቶ ቆመ፡፡ በዚያ
መሪነት ወደ ወሎ ክፍለ ሀገር አምባሰል አውራጃ ውስጥ ግሸን
ከምትባል አምባ መርቶ መስከረም 21 ቀን 1440 ዓ.ም
አደረሳቸው፡፡ በእውነትም ይህች ግሸን የተባለችው አምባ
ጥበበኛ ሰው እንደቀረጻት የተዋበች መስቀለኛ ቦታ ሆና
ስላገኟት የልባቸው ስለደረሰ ደስ አላቸው፡፡ እግዚአብሔር ገና
ዓለምን ሲፈጥር የግሸንን ዓምባ ለዚህ ክብር የተዘጋጀች አድርጎ
ፈጥሯታልና፡፡ በዚያም አምባ ታላቅ ቤተ መቅደስ ሠርተው
ቅዱስ መስቀሉንና ሌሎች ንዋየ ቅዱሳቱን በየመዓረጋቸው
የክብር ቦታ መድበው አስቀመጡዋቸው፡፡ ዘመኑም በ14ኛው
ክፍለ ዘመን ነው፡፡ የንግሥት ዕሌኒ ረድኤት በረከቷ ይደርብን
በጸሎቷ ይማረን፡፡ የመስቀሉ ፍቅር ይደረብን!

Sunday, May 15, 2016

=>+*"+<+>+ግንቦት 8+<+>+"*+

አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
አሜን
ግንቦት 8
+ አርባ ዓመት በአስቄጥስ ገዳም ሲኖር ከቅጠል በቀር
ተመግቦ የማያውቀው የገዳመ አስቄጥሱ ገድለኛው አባት አቡነ
ዳንኤል የዕረፍቱ ዓመታዊ መታሰቢያ በዓሉ ነው፡፡
+ ሰማዕቱ አቡነ ዮሐንስ ከ224 ማኅበርተኞቹ ጋር
ምስክርነቱን በድል ፈጸመ፡፡
ሰማዕቱ አቡነ ዮሐንስ፡- ይህንንም ቅዱስ ግብፅ ስንሑት
በምትባል ሀገር በ14 ዓመቱ የአባቱን በጎች ሲጠብቅ
የእግዚአብሔር መልአክ ተገልጦለት እየመራው ወስዶ ከገዳም
አስገባው፡፡ ሃይማኖትን ጠንቅቆ ከተማረ በኋላ በ21 ዓመቱ
መንኩሶ ተጋድሎውን ጀመረ፡፡
ቅዱስ ዮሐንስ በገዳም በተጋድሎ ሲኖር መልአኩ ድጋሚ
ተገልጦለት የብርሃን አክሊል አሳይቶ ወደ አትሪብ ከተማ ሄዶ
በክርስቶስ ስም ሰማዕት እንዲሆን ነገረው፡፡ በጥሪውም
መሥረት እናትና አባቱን ተሰናብቶ ወደ አትሪብ ሄዶ በከሃዲው
መኰንን ፊት የክርስቶስን አምላክነት መመስከር ጀመረ፡፡
ብዙዎቹ የመኰንኑ ወታደሮች በእርሱ እምነት አመኑ፡፡ ነገር
ግን መኰንኑና ክፉዎች ተባብረው በልዩ ልዩ ዓይነት መንገድ ጽኑ
መከራን አደረሱበት፡፡ መልአኩም እየተገለጠ እያጽናናው
ቁስሎቹን ይፈውስለት ጀመር፡፡ መኰንኑም ወደ እንዴና ሀገር
ላከውና በዚያም እጅግ አሠቃዩት፡፡ በተአምራትም ብዙዎችን
አሳመነ፡፡ የእንዴናውም መኰንን ማሠቃየት በሰለቸው ጊዜ
ግንቦት 8 ቀን አንገቱን በሰይፍ አስቆረጠውና ሰማዕትነቱን
በድል ፈጽሞ የክብር አክሊልን ተቀዳጀ፡፡ ማኅበርተኞቹ የሆኑ
224 ሰዎችም ከእርሱ ጋር ተሰይፈው ዐረፉ፡፡ በቅዱስ
ዮሐንስም በመቃብሩም ላይ 12 ቀን ሙሉ ቀስተ ደመና
ተተክሎና መቃብሩን ሸፍኖት ታይቷል፡፡ የቅዱስ ዮሐንስ
ረድኤት በረከቱ ይደርብን በጸሎቱ ይማረን፡፡
+ + + + + + + + + + + + + + +
የገዳመ አስቄጥሱ አባ ዳንኤል፡- በመቃርስ ገዳም በደብረ
ሲሐት ይኖር የነበረ ሲሆን እርሱም እጅግ ገድለኛ አባት ነው፡፡
40 ዓመት በአስቄጥስ ገዳም ሲኖር ከቅጠል በቀር ተመግቦ
አያውቅም፡፡ በአስቄጥስ ገዳም ዜናው ሁሉ በዓለም በተሰማ
ጊዜ የነገሥታት ልጆችም ወደ እርሱ እየመጡ እየተባረኩ ይሄዱ
ነበር፣ ግማሾቹም በዚያው ይመነኩሱ ነበር፡፡ ይህም አባ
ዳንኤል ስሟን እንጣልዮስ አስብላ የነበረች ንግሥት
የነበረችውን ቅድስት በጥሪቃን የገነዛት ነው፡፡ እርሷም ወንድ
የነበረች ሲሆን ይህም የታወቀው ከሞተች በኋላ ነው፡፡
አውሎጊስ የሚባለውን የወፍጮ ድንጋይ እየወቀረ በመሸጥ
ለድኆች የሚመጸውትን ጻድቅ ሰው ዋስ እሆነዋለሁ በማለት
ከእግዚአብሔር ዘንድ ለምኖ ሥልጣንና ብዙ ወርቅ እንዲያገኝ
ያደረገው ይህ አባ ዳንኤል ነው፡፡ በኋላም አውሎጊስ ሀብቱና
ንብረቱ ከእግዚአብሔር የሚያርቀው ቢሆን አባ ዳንኤል
በጸሎቱ መልሶ ሀብቱን እንዲያጣ አድርጎታል፡፡
አውሎጊስ የሚባል ጻድቅ የወፍጮ ድንጋይ እየወቀረ
(እየጠረበ) በመሸት የሚየገኘውን ለድኆችና ጦም አዳሪዎች
ይመጸውት ነበር፡፡ አባ ዳንኤልም የአውሎጊስን መልካም ሥራ
ተመልክቶ እጅግ ደስ ብሎት ለአውሎጊስ የሀብቱን መጠን
እንዲጨምርለትና ይበልጥ እንዲመጸውት በማሰብ ወደ
እግዚአብሔር በጸሎት አሳሰበ፡፡ ለአውሎጊስም ዋስ ሆነውና
ሀብቱ ተጨመረለት፡፡ አንድ ቀን የሚወቅረውን ድንጋይ
ሲፈቅል በሸክላ ዕቃ የተደፈነ ሙሉ ወርቅ አገኘ፡፡ ወደ
ቁስጥንጥንያም ከተማ ሄዶ ለንጉሡ አስረከበና የንጉሡ
የሠራዊት አለቃ ሆኖ ተሾመ፡፡ ከተሾመም በኋላ የቀድሞውን
የጽድቅ ሥራውን ተወ፡፡ አባ ዳንኤልም ስለ እርሱ ሰምቶ
ሊያየው ቢሄድ በፈረስ ላይ ተቀምጦ በሠራዊት ታጅቦ በትዕቢት
ተመልቶ አገኘው፡፡ ክፉ የትዕቢት መንፈስ አድሮበት ነበር፡፡ አባ
ዳንኤልም አውሎጊስ ሀብት እንዲያገኝ በመለመኑ አዘነ፡፡
በሌሊትም የአውሎጊስ ነፍስ በእርሱ ምክንያት እንደጠፋች ራሱ
አባ ዳንኤልም ሲሰቀልና እመቤታችን ስለ እርሱ ስትማልድ
ራእይ አየ፡፡ ከእንቅልፉም በቃ ጊዜ የአውሎጊስ ሀብት
እንዲጠፋና ወደ ቀደመ ግብሩ እንዲመለስ በጾም ጸሎት ሱባኤ
ያዘ፡፡ መልአክም ተገልጦለት በእግዚአብሐር የፍርድ ሂደት
ውስጥ ጣልቃ በመግባቱ ከገሠጸው በኋላ አውሎጊስም
ምሕረት እንደሚያገኝ ነገረው፡፡ አውሎጊስን የሾሸመው
ንጉሥም ሞተና ሌላ ንጉሥ ነገሠ፡፡ አውለጊስንም ንብረቱን
ሁሉ ቀምቶ ነፍሱንም ለመግደል አሳደደው፡፡ አውሎጊስም
ነፍሱን ለማዳን ሽሽቶ ወደ ሀገሩ በመግባት የቀድሞ ሥራውን
መሥራት ጀመረ፡፡ ነዳያንንም እንደዱሮም መመገብ ጀመረ፡፡
አባ ዳንኤል ከታለቁ ጻድቅ ንጉሥ ከቅዱስ አኖሬዎስ ጋር
የተገናኘ ታሪክ አለው፡፡ ይኸውም አባ ዳንኤል 40 ዓመት ሙሉ
በአስቄጥስ ገዳም ሲኖር ከቅጠል በቀር ተመግቦ አያውቅም
ነበርና ከጽድቁና ከብቃቱ የተነሣ ከብዙ ዘመን በኋላ የመመካት
ክፉ ሀሳብ መጣበት፡፡ ‹‹በገዳም ውስጥ እንደእኔ ትርሕምትን
ገንዘብ ያደረገ ይኖር ይሆን?›› ብሎም አሰበ፡፡ ሰውን ወዳድ
የሆነ ጌታችንም ይህን ክፉ ሀሳቡን ሊያርቅለት ሽቶ ብርሃናዊ
መልአኩን ላከለት፡፡ መልአኩም አባ ዳንኤልን ስለ ትምክህቱ
ቢቆጣውም አባ ዳንኤል መልአኩን መልሶ ‹‹ጌታዬ ከእኔ
የሚሻል ካለ ንገረኝ፣ ወደ እርሱ ሄጄ አየው ዘንድ እወዳለሁ፣
በመመካቴም ወደ ፈጣሪዬ በልመና እመለስ ዘንድ›› አለው፡፡
መልአኩም ‹‹እግዚአብሔርን የሚፈራ ሰው የሮሜና
የቁስጥንጥንያ ንጉሥ አኖሬዎስ በመንግሥተ ሰማያት
ባልንጀራህ ነው›› አለው፡፡
‹‹ንጉሥ አኖሬዎስም የመነኮሳትን ሥራዎች ሁሉ ስለሚሠራ
ከልብሰ መንግሥቱ ሥር በሥጋው ላይ ማቅ ይለብስ ነበር››
ተብሎ በስንክሳሩ ላይ የተጻፈለት ጻድቅ ንጉሥ ሲሆን
ሰማያውያን የሆኑ ቅዱሳን መላእክትም ቅድስናውን
የመሰከሩለት በንግሥና ያለ ታላቅ የእግዚአብሔር አገልጋይ
ነው፡፡ አባ ዳንኤልም ይህ በሰማ ጊዜ መሬት ላይ ወድቆ
በራሱም ላይ አመድ ነስንሶ የዚህን የሮም ንጉሥ አኖሬዎስን
ግብር ያሳየው ዘንድ ጌታችንን ለመነ፡፡ ደመናም መጥታ ነጥቃ
ወሰደችውና ንጉሥ አኖሬዎስ ደጅ አደረሰቸውና ንጉሡን በዙፋኑ
ላይ ሆኖ ባየው ጊዜ ከግርማው የተነሣ አይቶት በታላቅ ፍርሃት
ውስጥ ሆኖ ከእግሩም በታች ሰገደለትና አኗኗሩንም ይነግረው
ዘንድ በጌታችን ስም አማፀነው፡፡ ንጉሥ አኖሬዎስም ሰሌን
በመታታት በእጅ ሥራው ደክሞ ከሚያገኘው በቀር ምንም
ሳይበላና ሳይለብስ 40 ዓመት እንደሆነው፣ ሰሌን ታቶ ሸጦ
ካገኘውም ውስጥ ከዕለት ምግቡ መግዣ የሚተርፈውን
ለድኆችና ለጦም አዳሪዎች እንደሚመጸውት፣ ምግቡም
እንጀራና ጨው፣ ቅጠል መጻጻም እንደሆነ፣ የማንንም ንብረት
ፈጽሞ እንዳልንካ፣ ድንግልናውንም ጠብቆ እንደሚኖር
ነገረው፡፡ አባ ዳንኤልም ድጋሚ ከእግሩ ሥር ወድቆ ሰግዶለት
ስለ ትምክህቱም ፈጽሞ እያዘኑ ወደ በዓታቱ ተመልሷል፡፡
አባ ዳንኤል አንድ ቀን ከረድኡ ጋር ወደ እስክንድርያ ሲጓዝ
ስሙ ምህርካ የሚባል እብድ አገኘ፡፡ ብዙ እብዶችም ይከተሉት
ነበር፡፡ እርሱም ለአገሩ ሰዎች ሁሉ በእውነት ያበደ ይመስላቸው
ነበር፡፡ አባ ዳንኤልም እጁን ይዞ ወደ ሊቀ ጳጳሳቱ ወስዶ
ትሩፋቱን ተጋድሎውን ነገረው፡፡ ከሊቀ ጳጳሳቱም ጋር ሆነው
እብዱን ስለራሱ እንዲነግራቸው በእግዚአብሔር ስም ባማሉት
ጊዜ ከዝሙት ጦር በመሸሽ ራሱን እብድ እንዳስመሰለ
ነገራቸው፡፡
አንድ ቀን አባ ዳንኤል በሌሊት በበረሃ ውስጥ በጨረቃ ብርሃን
ሲጓዝ በተራራ ላይ ቀምጣ ጠጉሯ መላ ሰውነቷን የሸፈናት
በዚያም በረሃ ስትኖር በተሰነጠቀ ዓለት ውስጥ 38 ዓመት
ብቻዋን ማንም ሳያያት የኖረች ጻድቅ እናት አግኝቶ ምሥጢሯን
ሁሉ ነግራዋለች፡፡ እርሷም ቅድስት አመተ ክርስቶስ ናት፡፡ አባ
ዳንኤልም 38 ዓመት ሙሉ በዚህ በረሃ ምንም ሰው ሳታይ
የኖረችበትን ተገድሎዋን በዝርዝር ነግራቸዋለች፡፡ እርሳቸውም
ወደ ገዳማቸው ተመልሰው ለአበ ምኔቱና ለመነኮሳቱ ታሪኳን
በመንገር ልብስ ይዘውላት ቢመጡ ዐርፋ አግኝተዋታል፡፡
አባ ዳንኤል የልዮንን የክህደት ደብዳቤ ወታደሮቹ አምጥተው
በመነኮሳቱ ፊት ሲያነቡ ደብዳቤውን ተቀብሎ በሕዝቡ ፊት
ቀዶታል፡፡ ወታደሮቹም አባ ዳንኤልንደብደበው ከገዳሙም
አሳደውታል፡፡ ብዙ ሥቃይም አድርሰውበታል፡፡
አባ ዳንኤል በአንዲት ዕለት ከደናል ገዳም ደርሶ ደጁን አንኳኳ፡፡
እነርሱም አባ ዳንኤል መሆኑን ዐውቀው ከፈቱለት፡፡ አንዲት
ሴትም ራሷን ዕብድ አስመስላ በደጅ የምትተኛ ሴት ነበረች፡፡
እርሱም ዕብድ መስላ በደጅ ስለተቀበጠችው ሴት አበምነቷን
ሲጠይቃት እብድ መሆኗን ነገረችው፡፡ አባ ዳንኤል ግን ዕብድ
የመሰለቻቸው ሴት እብድ ሳትሆን በድብቅ በታላቅ ተጋድሎ
የምትኖር ቅድስት ሴት መሆኗን ነገራት፡፡ ዕብድ የተባለችውም
ሴትም አባ ዳንኤል ምሥጢሯን እንደገለጠባት በስውር ዐውቃ
ወዲያው ደብዳቤ ጽፋ ይኸውም ‹‹የተከበራችሁ እኅቶቼ
ስላስቀየምኳችሁና ስላሳዘንኳችሁ ይቅር በሉኝ›› ብላ ጽፋ
ደብዳቤውን አስቀምጣ ጥላቸው ጠፋች፡፡ እነርሱም ከዚያ በኋላ
ዳግመኛ አላዩአትም፡፡
ደናግል ወደሚኖሩበት ገዳም አንድ የወንበዴዎች አለቃ ሰይጣን
አነሳስቶት ወደ ገዳሙ በአባ ዳንኤል ተመስሎ ቆቡን ደፍቶ
በሩን አንኳኳ፡፡ ደናግላኑም ሊዘርፋቸው መምጣቱን ምንም
ባለማወቅ ይልቁንም አባ ዳንኤል መጣ ብለው በሩን
ከፈቱለትና አስገቡት፡፡ እግሩንም አጥበው ለበረከት ብለው
የእግሮቹን ዕጣቢ በፊታቸው ላይ ረጩት፡፡ ከመካከላቸውም
አንዷ ዐይነ ሥውር ነበረችና ዐይኗ ወዲያው በራላት፡፡ በዚህም
ደናግሉ እጅግ ተደስተው ‹‹አባ ዳንኤል አንተ ንዑድ ክቡድ ነህ››
ብለው ሰገዱለት፡፡ ይህን ጊዜ የሽፍቶቹ አለቃ በጣም ደንግጦ
በመጸጸት ወደ አባ ዳንኤል ዘንድ ሄዶ ያደረገውን ሁሉ በመናገር
ንስሓ ገባ፡፡ መንኩሶም በታላቅ ተጋድሎ መኖር ጀመረ፡፡
እርሱም ተአምራት እስከማድረግ ደርሶ በሰላም ዐረፈ፡፡ የአባ
ዳንኤልም ተጋድሎና ተአምር ምን ቢጽፉት የሚያልቅ
አይደለም፡፡ ዕረፍቱም በደረሰ ጊዜ ጌታችን ታላቅ ቃልኪዳን
ሰጥቶት ቅድስት ነፍሱን ወደ እርሱ ወስዷታል፡፡ የአባ ዳንኤል
ረድኤት በረከቱ ይደርብን በጸሎቱ ይማረን፡፡

=>+*"+<+>+ኢየሱስ ክርስቶስ ተማላጅ እንጂ አማላጅ አይደለም+<+>+"*+

“ያመኑትም ሕዝብ አንድ ልብ አንዲትም ነፍስ ነበሩአቸው”።
የሐ.ሥራ ፬፡፴፪
ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተማላጅ
እንጂ አማላጅ አይደለም::
የተሐድሶ መናፍቃኑ አንደበት “ክርስቶስ አማላጅ ነው” በማለት
በዛሬው ዕለት የእምነት አቋሙን የገለጹበት ጽሑፍ
አውጥቶዋል::
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን
#ጌታችን_መድኃኒታችን_ኢየ ሱስ_ክርስቶስን
#አምላክ_ወልደ_አምላክ_ብ ላ_ታምናለች፤
ታስተምራለችም:: ጌታችንና አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ
ክርስቶስ ተማላጅ እንጂ አማላጅ እንዳልሆነ ቅዱሳን መጻሕፍ
ይናገራሉ:: በዚህ በተሐድሶ ለወጣው የምንፍቅና ትምህርት
ምላሽ ይሆን ዘንድ የሚከተለውን የቤተ ክርስቲያናችን
አስተምህሮ የሚገልጽ ጽሑፍ አቅርበንላችኋል::
+++
ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የእርሱን
ማንነት ገልጦ ያስተማረበት ትምህርት ነው። በዚህም
ትምህርቱ፥ እርሱ የበጎች እረኛ እንደሆነ፥ የበረቱም በር እርሱ
መሆኑን ተናግሯል። እውነት የባህርይ ገንዘቡ ስለሆነም፥
ትምህርቱን «እውነት እውነት እላችኋለሁ፤» በማለት
ጀምሯል። በዚህም አማናዊ በሆነ ትምህርቱ «ወደ በጎች በረት
በበሩ የማይገባ፥ በሌላም በኲል የሚገባ ሌባ፣ ወንበዴም
ነው፤» ብሏል። ይኽንንም ስለ ሦስት ነገር ተናግሮታል።
፩ኛ፦ #ጌታችን_አምላካችን_መድኃ ኒታችን #ኢየሱስ_ክርስቶስ
፥ ከእናቱ ማኅፀን ጀምሮ ዕውር ሆኖ የተወለደውን ብላቴና
በምራቁ ጭቃ አድርጐ፥ በሰሊሆም ጠበልም እንዲጠመቅ
በማድረግ ፈጽሞ ስለፈወሰው፥ አይሁድ ብላቴናውንም
ወላጆቹንም አስቸግረዋቸው ነበር። ከፈሪሳውያን አንዳንዶቹ፦
«ይህ ሰው (ኢየሱስ) ከእግዚአብሔር አይደለም፥ ሰንበትንም
አይከብርምና፤» እያሉ ብላቴናውን ተከራክረውታል። እርሱ
ግን፦ «ኃጢአተኛ ሰው እንዲህ ያለ ተአምራት ማድረግ (በደረቅ
ግንባር ላይ ዓይን መፍጠር) እንዴት ይችላል? . . . እርሱ ነቢይ
ነው፤» አላቸው። ይኸውም፦ የነቢያት አለቃ ሙሴ፥
ከእግዚአብሔር አግኝቶ፥ «እግዚአብሔር ከወንድሞቻችሁ
መካከል (ከእናንተ ወገን) እንደ እኔ ያለ ነቢይ ያስነሣላችኋልና
እርሱን ስሙት፤» በማለት ለእስራኤል ዘሥጋ የነገራቸው ቃለ
ትንቢት ነው። የሐዋ ፯፥፴፯። ምክንያቱም በብዙ መንገድ
ሙሴ ለኢየሱስ ክርስቶስ ምሳሌ ነውና። የነቢያት አምላካቸው
ኢየሱስ ክርስቶስ «ነቢይ» መባሉም ነቢያት በአንድም ሆነ
በሌላ ምሳሌዎቹ በመሆናቸው ነው።
የብላቴናው ወላጆች ደግሞ አይሁድ ወጥረው በጠየቋቸው ጊዜ፥
«ይህ ልጃችን እንደሆነ፥ እውር ሆኖም እንደተወለደ
እናውቃለን። አሁን ግን እንዴት እንደሚያይ፥ ዓይኖቹንም ማን
እንደ አበራለት እናውቅም፥ እርሱን ጠይቁት፥ አዋቂ ነውና፥
ስለራሱም መናገር ይችላልና፤» አሉ። እንዲህም ማለታቸው
«እርሱ ክርስቶስ ነው፥ ብሎ በእርሱ የሚያምን ቢኖር
ከምኲራብ ይውጣ፤» የሚለውን የአይሁድን ዓዋጅ ፈርተው
ነው። ብላቴናው ግን ደጋግመው በጠየቁት ጊዜ «አትሰሙኝም
እንጂ ነገርኋችሁ፥ እንግዲህ ምን ልትሰሙ ትሻላችሁ? እናንተም
ደቀመዛሙርቱ ልትሆኑ ትሻላችሁን?» ብሎ ሳይፈራ
ተከራከራቸው። በዚህን ጊዜ «ራስህ በኃጢአት የተወለድህ አንተ
እኛን ታስተምራለህን?» ብለው ከምኲራብ አወጡት። በዚህም
ንግግራቸው በጌታ ቃል፦ «የእግዚአብሔር ሥራ ሊገለጥበት
ነው እንጂ እርሱ አልበደለም፥ ወላጆቹም አልበደሉም፤»
የተባለውን ሰው በልበ ደንዳናነት ኰነኑት። ከቤተ መቅደስም
አስወጡት። ዮሐ ፱፥፫። ጌታችንም አግኝቶት «አንተ
በእግዚአብሔር ልጅ ታምናለህን?» አለው። ብላቴናውም፦
«አቤቱ፥ አምንበት ዘንድ እርሱ ማነው?» ብሎ መለሰለት።
ጌታችን ኢየሱስም «የምታየው፥ ከአንተ ጋርም የሚነጋገረው
እርሱ ነው፤» አለው። ይኸውም «ነቢይ ነው፤» እንዳለ
በምሳሌው እንዳይቀር «አምላክ ወልደ አምላክ» ብሎ
እንዲያምን ነው። እርሱም «አቤቱ ፥ አምናለሁ፤» ብሎ
ሰገደለት። ከዚህ በኋላ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፦ «እኔ
የማያዩት እንዲያዩ (አላዋቆች ነን የሚሉ ሐዋርያት አዋቆች
ይሆኑ ዘንድ) የሚያዩትም እንዲታወሩ (አዋቆች ነን የሚሉ
ፈሪሳውያን አለዋቆች ይሆኑ ዘንድ) ለፍርድ መጥቻለሁ።
(ላመነብኝ ልፈርድለት ላላመነብኝ ልፈርድበት፥ ለሰው
መፈራረጃ ለመሆን ከሰማይ ወርጃለሁ)። አለው። በዚህን ጊዜ
ይኽንን የሰሙ ፈሪሳውያን፦ «እኛ ደግሞ ዕውሮች ነን?»
አሉት። ጌታችን ኢየሱስም ዕውሮችስ ብትሆኑ ኃጢአት
ባልሆነባችሁ ነበር፤ (ነውረ ሥጋ ከመንግሥተ ሰማይ
አያወጣምና)፤ አሁን ግን እናያለን (እናውቃለን) ትላላችሁ፥
አታዩምም፤ (አታውቁምም)፤ ስለዚህም ኃጢአታችሁ ጸንቶ
ይኖራል፤ (ንስሐ ስለማትገቡ ኃጢአታችሁ አይሰረይላችሁም)፤
አላቸው። ዮሐ ፱፥፩፥፵፩። እንግዲህ በዚህ ምክንያት «ለሰው
መፈራረጃ እሆን ዘንድ መጥቻለሁ።» በማለቱ፥ ለምሕረትም
እንደመጣ ለማጠየቅ በዮሐንስ ወንጌል በምዕራፍ አሥር
ያለውን አስተምሯል።
፪ኛ፦# ይህ_ዕውር_ሆኖ_ተወልዶ_ ጌታ #የፈወሰው_ብላቴና፥
ፈሪሳውያን፦ እንዴት እንዳየ ደጋግመው በጠየቁት ጊዜ፥ ደጋግሞ
እውነቱን ነግሯቸዋል። በተጨማሪም፦ «እናንተም ደቀ
መዛሙርቱ ልትሆኑ ትሻላችሁን?» ብሎም ጠይቋቸዋል።
እነርሱ ግን፥ «አንተ የእርሱ ደቀመዝሙር ሁን፥ እኛስ የሙሴ
ደቀመዛሙርት ነን። እግዚአብሔር ሙሴን እንደተነጋገረው
እናውቃለን፥ ይህን ግን ከወዴት እንደሆነ አናውቅም፤» አሉት።
በዚህን ጊዜ «. . . ከወዴት እንደሆነ፥ አታውቁምና እጅግ ድንቅ
ነው፤ ነገር ግን ዓይኖቼን አበራልኝ። ይህ ሰው ከእግዚአብሔር
ባይሆን ኖሮ ምንም ማድረግ ባለቻለም ነበር፤» ብሎአቸዋል።
እንግዲህ፦ «ከወዴት እንደሆነ አናውቅም፤» ብለውት ስለነበረ
ከወዴት እንደሆነ ለማጠየቅ አንቀጸ አባግዕን አስተምሯል።
፫ኛ፦ «ቸር እረኛ አይደለህም፤» ብለውት ስለነበር፥ ቸር እረኛ
መሆኑን ለማጠየቅ ነው። ይኽንንም፦ «ቸር ጠባቂ እኔ ነኝ፥
ቸር ጠባቂ ስለ በጎቹ ነፍሱን ይሰጣል። ጠባቂ ያይደለ፥ በጎቹም
ገንዘቡ ያይደሉ ምንደኛ ግን፥ ተኲላ ሲመጣ ባየ ጊዜ በጎቹን ትቶ
ይሻላል፤ ተኲላም መጥቶ በጎቹን ይነጥቃቸዋል፥
ይበትናቸዋልም። ምንደኛስ ይሸሻል፥ ስለ በጎቹም አያዝንም፥
ምንደኛ ነውና።» በማለት ነግሯቸዋል።
ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፦ በጎች
ያላቸው ምእመናንን ነው። የዕለተ ምጽአት ፍርድ እንዴት
እንደሆነ ለደቀመዛሙርቱ በነገራቸውም ጊዜ፥ ጻድቃንን በበጎች
መስሎ፥ «በጎቹን በቀኝ ያቆማቸዋል፤» ብሏል። ማቴ
፳፭፥፴፫። ቅዱስ ጴጥሮስንም፦ «በጎቼን ጠብቅ፤» ብሎታል።
ዮሐ ፳፩፥፲፭። ተኲላ ያለው ደግሞ ሰይጣንን እና መልክተኞቹን
ነው። ቅዱስ ዳዊት፦ በልዑል ረድኤት የሚያድር፥ በሰማይ
አምላክ ጥላ ውስጥ የሚቀመጥ፥ እግዚአብሔርን፦ «አንተ
መጠጊያዬና አምባዬ፥ አምላኬና ረዳቴ ነህ፥ በአንተ
እታመንብሃለሁ፤» የሚል ሰው፥ የሚያገኘውን ጸጋ ሲናገር፥
«ክፉ ነገር ወደ አንተ አይቀርብም፥ መቅሠፍትም ወደ ቤትህ
አይገባም። በመንገድህ ሁሉ ይጠብቁህ ዘንድ መላእክቱን ስለ
አንተ ያዝዛቸዋልና፥ እግርህም በድንጋይ እንዳትሰናከል
በእጆቻቸው ያነሡሃል። በተኲላና በእባብ ላይ ትጫናለህ፥
አንበሳውንና ዘንዶውን ትረግጣለህ፤» ብሏል። መዝ ፺፥፩-፲፫።
ካልተጠነቀቁ በስተቀር ተኲላት (መናፍቃን) አደገኞች ናቸው።
ይኽንንም ጌታችን «የበግ ለምድ ለብሰው ወደ እናንተ
ከሚመጡ ከሐሰተኞች ነቢያት (ከመናፍቃን) ተጠንቀቁ፥
በውስጣቸው ግን ነጣቂዎች ተኲላዎች ናቸው።» በማለት
ነግሮናል። ማቴ ፯፥፲፭። ከዚህም ሌላ «እነሆ እኔ እንደ በጎች
በተኲላዎች መካከል እልካችኋለሁ፤ . . . ከክፉዎች ሰዎች
ተጠበቁ፤» ብሎናል።
ተኲላ ተንኰለኛ አውሬ ነው፥ ተመሳስሎ ከበጎች ጋር መደባለቅ
ያውቅበታል፥ ሥጋ በል ሲሆን ሣር እንደሚነጭ እንስሳ
አንገቱን ቀብሮ ይውላል፥ ቢርበውም ምቹ ጊዜ እስኪያገኝ
ይታገሣል። በጎች በራሳቸው አቅም ይኽንን መከላከል
አይችሉም፥ ምክንያቱም የዋሃን ናቸውና። በመሆኑም ተግቶ
የሚጠብቅ እረኛ ያስፈልጋቸዋል። እረኛ ከሌላቸው ግን
ይጠፋሉ። ይኽንን በተመለከተ ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ
ከምእመናን ሕይወት ጋር በማገናዘብ፦ «እንደ በጎች ትቅበዘበዙ
ነበርና፥ አሁንም ወደ ነፍሳችሁ እረኛና ጠባቂ ተመለሱ፤»
ብሏል። ፩ኛ ጴጥ ፪፥፳፭። በጎች የምእመናን ብቻ ሳይሆን
የክርስቶስም ምሳሌዎች ናቸው። መጥምቀ መለኰት ቅዱስ
ዮሐንስ፦ «እነሆ የዓለምን ኃጢአት የሚያስወግድ
የእግዚአብሔር በግ፤» ያለው ለዚህ ነው። ዮሐ ፩፥፳፱። ነቢዩ
ኢሳይያስም፦ «እርሱ ግን በመከራው ጊዜ አፉን አልከፈተም፥
እንደ በግ ወደ መታረድ ተነዳ፥ የበግ ጠቦትም በሸላቾቹ ፊት
ዝም እንደሚል እንዲሁ አፉን አልከፈተም።» በማለት
አስቀድሞ ተናግሯል። ኢሳ ፶፫፥፯።
፩፥፩፦ #በበሩ_የሚገባና_የማይገባ ፤
#በበሩ_የሚገባ_ማለት፦ ትንቢት ተነግሮለት፥ እግዚአብሔር
አብ መስክሮለት፥ ምእመናን ወደ አሉበት ወደ ኢየሩሳሌም
በመምሕርነት የሚመጣ ማለት ነው። ጌታችን አምላካችን
መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ ዓለም የመጣው
ትንቢት ተነግሮለት፥ ሱባዔ ተቆጥሮለት ነው። ኢሳ ፯፥፲፬፤ ፱፥፪-
፮፤ ፲፩፥፩። የባህርይ አባቱም በዮርዳኖስ፦ «በእርሱ ደስ
የሚለኝ የምወደው ልጄ ይህ ነው፤» በማለት መስክሮለታል።
ማቴ ፫፥፲፯። ከዚያም በፊት የልደቱን ብሥራት ለእመቤታችን
ለቅድስት ድንግል ማርያም የነገረ፥ ቅዱስ ገብርኤል፥
«ማርያም ሆይ፥ በእግዚአብሔር ዘንድ ባለሟልነትን
አግኝተሻልና አትፍሪ። እነሆ ትፀንሻለሽ፥ ወንድ ልጅንም
ትወልጃለሽ፥ ስሙንም ኢየሱስ ትይዋለሽ። እርሱም ታላቅ
ነው፥ የልዑል እግዚአብሔር ልጅም ይባላል፤» ብሏል። ሉቃ
፩፥፴-፴፪። በተወለደ ጊዜም ቅዱሳን መላእክት፥ ለእረኞች
ተገልጠው፥ «እነሆ፥ ለእናንተና ለሕዝቡ ሁሉ ደስታ የሚሆን
ታላቅ የምሥራች እነግራችኋለሁና አትፍሩ፤ እነሆ፥ ዛሬ በዳዊት
ከተማ መድኅን ተወልዶላችኋል፥ ይኸውም ቡሩክ ጌታ ክርስቶስ
ነው።» በማለት መስክረውላቸዋል። ሉቃ ፪፥፲፥፲፩።
መጥምቀ መለኰት ቅዱስ ዮሐንስም፦ «ጫማውን እሸከም
ዘንድ ከማይገባኝ ከእኔ በኋላ የሚመጣው ግን ከእኔ ይልቅ
ይበረታል፥እርሱ በእሳትም በመንፈስ ቅዱስም ያጠምቃችኋል፤
መንሹም በእጁ ነው፥ አውድማውንም ፈጽሞ ያጠራል፥
ስንዴውን በጎተራ ይከታል፥ ገለባውን በማይጠፋ እሳት
ያቃጥለዋል።» ማቴ ፫፥፲፩። «ተጐንብሼ የጫማውን ጠፍር
መፍታት ከማይገባኝ ከእኔ የሚበረታ በኋላዬ ይመጣል።» ማር
፩፥፯፣ ሉቃ ፫፥፲፭። «ዳሩ ግን እናንተ
የማታውቁት በመካከላችሁ ቆሞአል፤ እኔ የጫማውን ጠፍር
ልፈታ የማይገባኝ፥ ከእኔ በኋላ የሚመጣው ከእኔ ይልቅ
የሚከብር ይህ ነው። . . . አንድ ሰው ከእኔ ይልቅ የከበረ
ሆኖአል ብዬ ስለ እርሱ ያልሁት ይህ ነው። እኔም አላውቀውም
ነበር፥ ነገር ግን ለእስራኤል ይገለጥ ዘንድ ስለዚህ በውኃ
እያጠመቅሁ መጣሁ።» ዮሐ ፩፥፳፮። «ከሰማይ ካልተሰጠው
ሰው አንዳች ሊቀበል አይቻለውም። እናንተ እኔ ክርስቶስ
አይደለሁም፥ ነገር ግን ከእርሱ በፊት ተልኬአለሁ እንዳልሁ
ራሳችሁ ትመሰክሩልኛላችሁ። ሙሽራይቱ ያለችው እርሱ
ሙሽራ ነው፥ ቆሞ የሚሰማው ሚዜው ግን በሙሽራው ድምፅ
እጅግ ደስ ይለዋል። እንግዲህ ይህ ደስታዬ ተፈጸመ። እርሱ
ሊልቅ እኔ ግን ላንስ ይገባል።» ብሏል። ዮሐ ፫፥፳፯።
ከእግዚአብሔር አብ፥ ከነቢያት ትንቢት፥ ከቅዱሳን መላእክት
ብሥራትና የምሥራች፥ እንዲሁም ከመጥምቀ መለኰት ቅዱስ
ዮሐንስ ምስክርነት እንደተማርነው፦ ጌታችን አምላካችን
መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፦ በበሩ የገባ ቸር እረኛ ነው።
በመሆኑም «ለእርሱ በረኛው ይከፍትለታል፥ በጎቹም ቃሉን
ይሰሙታል፥ እርሱም በጎቹን በየስማቸው ይጠራቸዋል፥
አውጥቶም ያሰማራቸዋል።» ብሎአል። በረኛ የተባለ መንፈስ
ቅዱስ ነው፤ ሕዋሳቱን በሰበሰበ፥ ዐሠርቱ ቃላትን በያዘ፥ በሰቂለ
ኅሊና፥ በነቂሐ ልቡና በሚኖር ሰው የሚያድር እርሱ ስለሆነ
የሰውን አእምሮ ለበጎ ይከፍተዋል። አንድም በረኛ የተባለ ራሱ
ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። ምክንያቱም፥ ለጊዜው አምስት ሺ
አምስት መቶ ዘመን የተዘጋች ገነትን በቤዛነቱ የሚከፍት፥
ለፍጻሜውም በዕለተ ምጽአት መንግሥተ ሰማያትን የሚከፍት
እርሱ ነውና። «በጎቹ ቃሉን ይሰሙታል፥» እንዳለ፥ አሥራ ሁለቱ
ሐዋርያት፥ ሰባ ሁለቱ አርድእት፥ ሠላሳ ስድስቱ ቅዱሳት አንስት
ትምህርቱን ተቀብለውታል። በየስማቸውም ዮሐንስ፥ ያዕቆብ፥
ስምዖን፥ ታዴዎስ፥ ዲዲሞስ፥ ቶማስ እያለ ጠርቶአቸዋል።
«አውጥቶም ያሰማራቸዋል፤» የተባለው ደግሞ፦ «በጠባቢቱ
በር ግቡ፤ . . . እኔን ሊከተል የሚወድ ራሱን ይካድ፥ ጨክኖም
የሞቱን መስቀል ተሸክሞ ይከተለኝ፤» እያለ ያስተምራቸዋል
ማለት ነው። መሰማሪያ የተባለው ትምህርተ ወንጌል ነው፥
አንድም መከራ ነው፥ አንድም በመጨረሻ የሚወርሱት ክብረ
መንግሥተ ሰማያት ነው።
ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሦስት
ዓመት ከሦስት ወር ካስተማራቸው በኋላ ይሰቀልላቸዋል
(ነፍሱን አሳልፎ ይሰጥላቸዋል)። «በጎቹም ይከተሉታል»፤
እርሱን አብነት አድርገው ወንጌልን ያስተምራሉ፥ መከራን
ይቀበላሉ፥ በመከራ ይመስሉታል። «ቃሉን ያውቃሉና።»
ትምህርቱን ተቀብለውታልና። «ሌላውን ግን ይሸሹታል እንጂ
አይከተሉትም፥ የሌላውን ቃሉን አያውቁምና።» ትንቢት
ሳይነገርለት፥ መጻሕፍት ሳይመሰክሩለት የመጣውን ግን ሌባ
ወንበዴም በመሆኑ አብነት አያደርጉትም፥ አይመስሉትም፤
ይነቅፉታል፥ ያወግዙታል እንጂ ትምህርቱን አይቀበሉም።
ጌታችን ይኽንን ምሳሌ ቢነግራቸውም እረኛ የተባለ እርሱ፥
አባግዕ የተባሉ ደግሞ እነርሱ እንደሆኑ አልገባቸውም።
ዳግመኛም ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ
ክርስቶስ፥ «እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ የበጎች በር እኔ ነኝ።
ከእኔ በፊት የመጡ ሁሉ ሌቦችና ወንበዴዎች ናቸው፥ ነገር ግን
በጎች አልሰሙአቸውም። እውነተኛው የበጎች በር እኔ ነኝ፥ በእኔ
በኲልም የሚገባ ይድናል፤» (ወደ ሃይማኖት ወደ ወንጌል
ይገባል)፤ «ይወጣልም፤» (ከፈቃደ ሥጋ ይወጣል፤ አንድም በጎ
ሥራ ለመሥራት ለማስተማር ይወጣል)፤ መሰማሪያም
ያገኛል። (መከራን ማለትም እስራቱን፣ ግርፋቱን፣ እሳቱን፣
ስለቱን፣ ያገኛል)። አንድም በጉባኤ ምእመናንን ያገኛል፤
አንድም ክብረ ሥጋን ክብረ ነፍስን ያገኛል)። ሌባ ግን ሊሰርቅና
ሊያርድ፥ ሊያጠፋም ካልሆነ በቀር አይመጣም። (ሌባው
ወንበዴው ግን በነፍስም በሥጋም ሊጐዳ ሊያጠፋ ነው እንጂ
ሊያለማ ሊጠቅም አይመጣም)። እኔ ግን የዘለዓለም ሕይወትን
እንዲያገኙ፥ እጅግም እንዲበዛላቸው መጣሁ።» አላቸው።
በበሩ የማይገባ ማለት ደግሞ፦ ትንቢት ሳይነገርለት፥ ሱባዔ
ሳይቆጠርለት፥ እግዚአብሔር አብ ሳይመሰክርለት፥ ቅዱሳን
መላእክትም ብሥራቱንም የምሥራቹንም ሳይናገሩለት የመጣ
ማለት ነው። ይኸውም እንደ ይሁዳ ዘገሊላ አንድም እንደ
ቴዎዳስ ዘግብፅ ነው። የአይሁድ ሸንጎ በቅዱሳን ሐዋርያት
ተቆጥተው ሊገድሉአቸው በወደዱ ጊዜ፥ በሕዝቡ ሁሉ ዘንድ
የከበረ ስሙ ገማልያል የሚባል የኦሪት መምህር ነበረ።
እርሱም ቅዱሳን ሐዋርያትን ፈቀቅ እንዲያደርጉአቸው ካዘዘ
በኋላ፥ «እናንተ የእስራኤል ሰዎች ሆይ፥ በእነዚህ ሰዎች
በምታደርጉት ነገር ለራሳችሁ ተጠንቀቁ። ቀድሞም ከዚህ
ዘመን በፊት ቴዎዳስ ተነሥቶ ራሱን ከፍ ከፍ አደረገ፤ (እኔ
አምላክ ነኝ አለ)፤ አራት መቶ ሰዎችም ተከተሉት፥ ነገር ግን
እርሱም ጠፋ፥ የተከተሉትም ሁሉ ተበታተኑ፥ እንደ ኢምንትም
ሆኑ። ከእርሱም በኋላ ሰዎች ለግብር በተቈጠሩበት ወራት
ገሊላዊ ይሁዳ ተነሣ፥ ብዙ ሕዝብም ተከተሉት፥ እርሱም ሞተ፥
የተከተሉትም ሁሉ ተበታተኑ። አሁንም እላችኋለሁ፥ ከእነዚህ
ሰዎች (ከቅዱሳን ሐዋርያት) ራቁ፥ ተዉአቸውም፥ ይህ
ምክራቸው ይህም ሥራቸው ከሰው የተገኘ ከሆነ ያልፋል፥
ይጠፋልም። ከእግዚአብሔር የመጣ ከሆነ ግን ልታፈርሱት
አትችሉም፥ ከእግዚአብሔርም ጋር እንደሚጣላ አትሁኑ።»
ብሎአል። የሐዋ ፭፥፴፬፥፴፱።
፩፥፪፦ #ቸር_ጠባቂ_እኔ_ነኝ፤
ቅዱስ ዳዊት እግዚአብሔር እረኛ ጠባቂ መሆኑን ሲናገር፦
«እግዚአብሔር ይጠብቀኛል፥ የሚያሳጣኝም የለም።
በለመለመ መስክ ያሳድረኛል፥ በዕረፍት ውኃ ዘንድ አሳደገኝ፤»
ብሎአል። መዝ ፳፪፥፩። ቸር እረኛ የጠፋውን በግ እስኪያገኘው
ድረስ ይፈልገዋል። ይኽንንም፦ «የሰው ልጅ (ወልደ ዕጓለ
እመሕያው ክርስቶስ) የጠፋውን ሊፈልግና ሊያድን
መጥቶአልና። ምን ትላላችሁ? መቶ በጎች ያለው ሰው ቢኖር፥
ከመካከላቸውም አንዱ ቢጠፋው፥ ዘጠና ዘጠኙን በተራራ ላይ
ትቶ የጠፋውን ሊፈልግ ይሄድ የለምን? እውነት እላችኋለሁ፥
ባገኘው ጊዜ ካልጠፉት ከዘጠና ዘጠኙ ይልቅ ጠፍቶ ስለተገኘው
ፈጽሞ ደስ ይለዋል፤» በማለት ነግሮናል። ማቴ ፲፰፥፲፩-፲፫።
እግዚአብሔር ቅዱሳን መላእክትን የፈጠራቸው በነገድ መቶ
አድርጎ ነበር። አንደኛው ነገድ (የሳጥናኤል ነገድ) በክህደት
በመጉደሉ ምክንያት አዳም መቶኛ ሆኖ ተቈጥሯል።
በመሆኑም የጠፋው በግ የተባለው አዳም ነው። ነቢዩ
ኢሳይያስም፦ «እነሆ እግዚአብሔር በኃይሉ ይመጣል፥
በክንዱም (በሥልጣኑ፥ በባህርይ ልጁ በኢየሱስ ክርስቶስ)
ይገዛል፥ እነሆ ዋጋው ከእርሱ ጋር ሥራውም በፊቱ ነው።
መንጋውን እንደ እረኛ ይመራል፥ ጠቦቶቹን በክንዱ ሰብስቦ
በብብቱ ይሸከማል፥ የሚያጠቡትንም በቀስታ ይመራል።»
በማለት እርሱ አምላካችን የሕይወታችን እረኛ እንደሆነ
ተናግሯል። ኢሳ ፵፥፲፩። ነቢዩ ሕዝቅኤል ደግሞ፦ «ጌታ
እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ እነሆ እኔ ራሴ በጎቼን እሻለሁ፥
እጎበኛቸዋለሁ። ከአሕዛብም ዘንድ አወጣቸዋለሁ፥ ከሀገሮችም
ሁሉ እሰበስባቸዋለሁ፥ ወደ ገዛ ሀገራቸውም አመጣቸዋለሁ፥
በእስራኤልም ተራሮች ላይ፥ በፈሳሾችም አጠገብ፥ በምድርም
ላይ ሰዎች በሚኖሩባት ስፍራ ሁሉ አሰማራቸዋለሁ።
በመልካም ማሰማርያ አሰማራቸዋለሁ፥ ጉሮኖአቸውም
በረዥሞቹ በእስራኤል ተራሮች ላይ ይሆናል፥ በዚያ በመልካም
ጉረኖ ውስት ይመሰጋሉ፥ በእስራኤልም ተራሮች ላይ በለመለመ
መሰማሪያ ይሰማራሉ። እኔ ራሴ በጎቼን አሰማራለሁ፥
አስመስጋቸውማለሁ፤ እኔም እግዚአብሔር እንደሆንሁ
ያውቃሉ፥ ይላል ጌታ እግዚአብሔር። የጠፋውንም እፈልጋለሁ፥
የባዘነውንም እመልሳለሁ፥ የተሰበረውንም እጠግናለሁ፥
የደከመውንም አጸናለሁ፥ የወፈረውንና የበረታውንም
እጠብቃለሁ፥ በፍርድም እጠብቃቸዋለሁ።» ብሏል። ሕዝ
፴፬፥፲፩-፲፮።
ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በጎቹን
ፍለጋ የመጣ ቸር እረኛ በመሆኑ፥ «ቸር ጠባቂ እኔ ነኝ፥ ቸር
ጠባቂ ስለ በጎቹ ነፍሱን ይሰጣል። ጠባቂ ያይደለ፥ በጎቹም
ገንዘቡ ያይደሉ ምንደኛ ግን ተኲላ ሲመጣ ባየ ጊዜ በጎቹን ትቶ
ይሸሻል፥ ተኲላም መጥቶ በጎቹን ይነጥቃቸዋል፥
ይበትናቸዋልም። ምንደኛስ ይሸሻል፥ ስለ በጎቹም አያዝንም፥
(የምእመናን ጥፋት አያሳዝነውም)፥ ምንደኛ ነውና። (ሥጋዊ፥
ዓለማዊ በመሆኑ መናፍቅ ጳጳስ፥ አላዊ ንጉሥ በተነሣ ጊዜ
ይክዳል፤ ምዕመናንን አሳልፎ ይሰጣቸዋል፥ ሐሰተኛ ነውና)።
ቸር ጠባቂ (እውነተኛ መምህር) እኔ ነኝ፥ የእኔ የሆኑትን
መንጋዎቼን (ወልድ ዋሕድ ብለው ያመኑብኝን) አውቃለሁ፥
የእኔ የሆኑትም ያውቁኛል፤ (በእኔ ያመኑብኝ እኔን አብነት
አድርገው መከራን ይቀበላሉ)፤ ብሏል።
፩፥፫፦ #አብ_እኔን_እንደሚያውቀኝ _እኔም_አብን
#አውቀዋለሁ፤
አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ ህልዋን ናቸው። አብ በወልድ
በመንፈስ ቅዱስ ህልው ነው፥ ወልድም በአብ በመንፈስ ቅዱስ
ህልው ነው፥ መንፈስ ቅዱስም በአብ በወልድ ህልው ነው።
«እኔ በአብ እንዳለሁ፥ አብም በእኔ እንዳለ እመኑ፤» ብሏል።
ዮሐ ፲፩፥፲፩። በስም በአካል በግብር ሦስት የሆኑ ሥላሴ
በህልውና አንድ እንደሆኑ ሁሉ በመለኰት፥ በሥልጣን፥
በባህርይ፥ በፈቃድ አንድ ናቸው። «እኔና አብ አንድ ነን፤» ያለው
ለዚህ ነው። ዮሐ ፲፥፴። እንግዲህ፥ አይሁድ በክፋታቸው «ይህ
ከወዴት እንደመጣ፥ ማን እንደሆነ አናውቅም፤» ብለውት
ስለነበረ፥ እናንተ ባታውቁኝ የባህርይ አባቴ አብ ያውቀኛል፥
እንደማለት፥ «አብ እኔን እንደሚያውቀኝ እኔም አብን
አውቀዋለሁ፤» ብሎባቸዋል። ይኸውም፦ «እኔ ልሰቀል ልሞት
መምጣቴን አብ እንደሚያውቅ ሁሉ እኔም የመጣሁበትን
ዓላማ አውቃለሁ፤» ሲል ነው። ለዚህ ነው ከዚያው አያይዞ፥
«ለበጎችም ቤዛ አድርጌ ሰውነቴን አሳልፌ እሰጣለሁ፤»ያለው።
በማቴዎስ ወንጌልም፦ «ከአብ በቀር ወልድን የሚያውቀው
የለም፤ (ያለ አብ ወልድን በባሕርዩ የሚያውቀው የለም፥
በባሕርይ አንድ ናቸውና)፤ አብንም ከወልድ በቀር፥ ወልድም
ሊገልጥለት ከሚፈቅደው በቀር የሚያውቅ ማንም የለም።
(ያለ ወልድ አብን በባሕርዩ የሚያውቀው የለም)፤» የሚል
አለ። ማቴ ፲፩፥፳፯።
ትንቢት ተነግሮለት፥ ሱባዔ ተቆጥሮለት፥ ወደዚህ ዓለም የመጣ
ቸር እረኛ ኢየሱስ ክርስቶስ፥ «ከዚህ ቦታ ያይደሉ ሌሎች
በጎችም አሉኝ፤ (በኢየሩሳሌም የሌሉ በአራቱ ማዕዘን ያሉ
ሌሎች አሉኝ)፤ ቃሌንም ይሰሙኛል፤ (ትምህርቴን
ይቀበሉኛል)፤ ለአንድ እረኛ አንድ መንጋም ይሆናሉ። (ለአንድ
ለክርስቶስ አካሉ ይሆናሉ፤ አንድም ለአንድ ሊቀ ጳጳስ አንድ
ማኅበር፥ አንድ ቤተሰብእ ይሆናሉ)፤ ብሎአል። ይህም ወደዚህ
ዓለም መምጣቱ ለቤተ አይሁድ ብቻ ሳይሆን ለመላው ዓለም
መሆኑን ያስተምረናል።
፩፥፬፦ #ሥልጣን_አለኝ፤
ነፍስንም ሥጋንም ከእመቤታችን ነስቶ (ወስዶ) በተዋሕዶ ሰው
የሆነ አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስ፥ ዓለምን ለማዳን መከራ
የተቀበለው፥ የሞተውም በፈቃዱ ነው። ይህም ይታወቅ ዘንድ፦
«ስለዚህም አብ ይወድደኛል፤» ካለ በኋላ «እንደ ገና አስነሣት
ዘንድ እኔ ነፍሴን እአጣለሁና። ከእኔ ማንም አይወስዳትም፤
ነገር ግን እኔ በፈቃዴ እሰጣታለሁ፥ እኔ ላኖራት ሥልጣን አለኝ፤
(ነፍሴን በገነት፥ ሥጋዬን በመቃብር ላኖራቸው ሥልጣን አለኝ)፤
መልሼ እወስዳት ዘንድ ሥልጣን አለኝ። (ነፍሴን ከሥጋዬ
አዋሕጄ በማስነሣት፥ በዕርገት፥ በየማነ አብ፥ በዘባነ ኪሩብ
አስቀምጣት ዘንድ ሥልጣን አለኝ)፤ ብሏል። መከራውን፥
ትንሣኤውን እና ዕርገቱን በተመለከተም ነቢያት አስቀድመው
ተናግረውታል።
- «እርሱ ስለ ኃጢአታችን ቈሰለ፥ ስለበደላችንም ታመመ፤
የሰላማችንም ተግሣጽ በእርሱ ላይ ነበረ፥ በእርሱም ቊስል እኛ
ተፈወስን። . . . እግዚአብሔርም ስለ ኃጢአታችን ለሞት
አሳልፎ ሰጠው።» ኢሳ ፶፫፥፭-፮።
- «እግዚአብሔርም ከእንቅልፍ እንደሚነቃ ተነሣ፤» መዝ
፸፯፥፷፭።
- «እግዚአብሔር በእልልታ፥ ጌታችንም በመለከት ድምፅ
አረገ።» መዝ ፵፮፥፭።
በመጨረሻ የምንመለከተው፥ ጌታችን አምላካችን
መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ «እውነተኛ የበጎች በር እኔ
ነኝ፤»ያለበትን ዋና ምክንያት ነው። ይኸውም በር የተከፈተለት
እንደሚገባ፥ የተዘጋበት ደግሞ በአፍአ እንደሚቀር ሁሉ፥
በጌታችን ያመነ የመንግሥተ ሰማያት በር ይከፈትለታል፥
ያላመነበት ደግሞ በሩ ተዘግቶበት በአፍአ እንደሚቀር ነው።
በመሆኑም በር የተባለው በእርሱ ላይ ያለን እምነት እንደሆነ
ከትርጓሜው እንረዳለን። የበሩንንም ቊልፍ ለቅዱሳን
አስረክቧል። ይኸውም ይታወቅ ዘንድ ቅዱስ ጴጥሮስን «አንተ
ብፁዕ ነህ፥ በሰማይ ያለው አባቴ ነው እንጂ ሥጋና ደም ይህን
አልገለጠልህምና። እኔም እልሃለሁ፥ አንተ ዐለት ነህ፥ በዚያች
ዐለት ላይም ቤተክርስቲያኔን እሠራታለሁ፥ የሲኦል በሮችም
(ደጅ ጠባቂ አጋንንት) አይበረቱባትም። የመንግሥተ ሰማያትም
መክፈቻ እሰጥሃለሁ፥ በምድር የምታስረው በሰማይ የታሰረ
ይሆናል፥ በምድርም የምትፈታው በሰማይ የተፈታ ይሆናል።»
ብሎታል። ማቴ ፲፮፥፲፯-፲፱። ሌሎችን ግን፦ «መንግሥተ
ሰማያትን በሰው ፊት ስለምትዘጉ ወዮላችሁ! እናንተም
አትገቡም፥ የሚገቡትንም ከመግባት ትከለክላላችሁ።»
ብሏቸዋል። ማቴ ፳፫፥፲፬። ስለዚህ በር በተባለ በኢየሱስ
ክርስቶስ ፈጽመን ልናምን ይገባል። እናምናለን ማለት ብቻም
ሳይሆን የምናምነውስ ማን እና ምን ብለን ነው ማለትም
ያስፈልጋል። ምክንያቱም ስሙን እየጠሩ፥ እንምንበታለን
እያሉ፥ ስለ እርሱ የሚያስተምሩት ትምህርት ፈጽሞ መስመር
የለቀቀባቸው ብዙዎች ናቸውና። የእኛ ግን መስመሩን
የጠበቀው ፍጹም እምነታችን እንደሚከተለው ነው።
፩ኛ፦ #ፈጣሪ_ነው፥ ብለን እናምንበታለን። «ሁሉም በእርሱ
ሆነ፥ (በእርሱ ተፈጠረ)፥ ከሆነውም (ከተፈጠረውም) ሁሉ ያለ
እርሱ ምንም የሆነ የለም። ዮሐ ፩፥፫።
፪ኛ፦ #የፈጠረውን_ፍጥረት_የሚገ ዛ_የባሕርይ አምላክ ነው።
«የእግዚአብሔር ልጅ እንደመጣ፤ እውነተኛም የሆነውን
እግዚአብሔርን እናውቅ አንድ ልቡናን እንደሰጠን እናውቃለን፤
እውነተኛውም በሆነው በእግዚአብሔር ልጅ በኢየሱስ ክርስቶስ
በማመን እንኖራለን፤ እርሱም እውነተኛ አምላክና የዘለዓለም
ሕይወት ነው።» ፩ኛ ዮሐ ፭፥፳።
፫ኛ፦# ፈጣሪ፥ የባሕርይ አምላክ በመሆኑም እግዚአብሔር
ነው። «በመጀመሪያ ቃል ነበረ፥ ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ
(በፈጣሪነት ከአብ ተካክሎ) ነበረ፤ ቃልም እግዚአብሔር ነበረ።
ይህም በመጀመሪያ በእግዚአብሔር ዘንድ (በፈጣሪነት
ከመንፈስ ቅዱስም ተካከልሎ) ነበረ። . . . ያም ቃል ሥጋ ሆነ፥
በእኛም አደረ፤ (ነፍስንና ሥጋን ነስቶ በተዋሕዶ ሰው ሆነ)።»
ዮሐ ፩፥፩፣ ፩። «አሁንም በገዛ ደሙ የዋጃትን
የእግዚአብሔርን ቤተክርስቲያን ትጠብቁ አንድ መንፈስ ቅዱስ
እናንተን ጳጳሳት አድርጎ ለሾመባት ለመንጋው ሁሉና ለራሳችሁ
ተጠንቀቁ፤» የሐዋ ፳፥፳፰።
፬ኛ፦ #ወልድ_በተለየ_አካሉ_ከሰ ማይ_ወርዶ፥ በተዋሕዶ ሰው
ሆኖ ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም በመወለዱ
በሥልጣን ከአብ ከመንፈስ ቅዱስ አላነሰም። «እኔና አብ አንድ
ነን፤» ዮሐ ፲፥፴። በሕልውናም አንድ ነው። «እኔ በአብ
እንዳለሁ አብም በእኔ እንዳለ እመኑ፤» ዮሐ ፩፥፲፩። «እኔን
የሚጠላ አቤን ይጠላል። . . . አሁን ግን እኔንም አባቴንም
አይተዋል፥ ጠልተውማል።» ዮሐ ፲፭፥፳፫።
፭ኛ፦ #ከእመቤታችን_ከቅድስት_ድ ንግል
#ማርያም_ከሥጋዋ_ሥጋ_ከነ ፍሷም_ነፍስ_ነስቶ የተወለደ
እርሱ የእግዚአብሔር የባሕርይ ልጅ ነው። «እነሆም፥ በእርሱ
ደስ የሚለኝ ልጄ ይህ ነው።» ማቴ ፫፥፩።
፮ኛ፦ #ሰው_የሆነው_በተዋሕዶ_ነ ው፥ በመሆኑም ከተዋሕዶ
በኋላ ሁለትነት የለም፥ ይህ የሥጋ ነው፥ ይህ ደግሞ የመለኰት
ነው ተብሎ መከፈል የለበትም። አብ «ልጄ ነው፤» ያለው
በተዋሕዶ አንድ አካል አንድ ባሕርይ የሆነውን ኢየሱስ
ክርስቶስን ነው። ወደ ሠርግ ቤት የተጠራውም ውኃውን ወደ
ወይን ጠጅ የለወጠውም ከተዋሕዶ በኋላ ሁለትነት የሌለበት
አንድ እርሱ ነው። ዮሐ ፪፥፩-፲። ሥጋን እንደተዋሐደ
ለማጠየቅ «አልዓዛርን የት ቀበራችሁት?» ያለም ከሞት
ያስነሣም አንድ እርሱ ነው። ዮሐ ፲፩፥፴፬፣፵፫። ከዚህም ሌላ
መቃብሩ ሳይከፈት ከመቃብር የወጣው (ሞትን ድል አድርጐ
የተነሣው) አንዱ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። ማቴ
፳፯፥፷፮፣፳፰፥፩። በተዘጋ ቤትም በሩ ሳይከፈት ከአንዴም ሁለት
ጊዜ የገባው አንዱ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። ዮሐ ፳፥፲፱፣፳፮።
፯፦ #ኢየሱስ_ክርስቶስ_ፈራጅ_ ዳኛ ነው። «አሁንም
በእግዚአብሔር ፊትና በመንግሥቱ በሚመጣበት ጊዜ፥
በሕያዋንና በሙታን ይፈርድ ዘንድ ባለው በጌታችን በኢየሱስ
ክርስቶስ እመክርሃለሁ። . . . እንግዲህስ የጽድቅ አክሊል
ይቆየኛል፥ ይህንም ጻድቅ ፈራጅ የሆነው እግዚአብሔር በዚያ
ቀን ለእኔ ያስረክባል።» ፪ኛ ጢሞ ፬፥፩፣፰።
፰፦ #እኛ_የምንለምነውን_በቅዱ ሳንም_ጸሎት
የምናስለምነውን ሁሉ እርሱ ያደርገዋል። «እኔ ወደ አብ
እሄዳለሁና፤ አብ በወልድ ይከብር (ይገለጥ) ዘንድ በስሜ
የምትለምኑትን ሁሉ አደርግላችኋለሁ። በስሜ የምትለምኑት
ነገር ቢኖር ያን አደርግላችኋለሁ።» ዮሐ ፲፬፥፲፪-፲፫።
እንግዲህ ሥጋን መዋሐዱን ለማጠየቅ የተናገረውን ቃል፥
አብነት ለመሆንም የሠራውን የትህትና ሥራ ሁሉ በትርጓሜ
እያስታረቅን በትክክለኛው እምነት ጸንተን ልንቆም ይገባናል።
በአምልኮታችን ሁሉ ኢየሱስ ክርስቶስን፥ እንደ ቅዱስ
እስጢፋኖስ፥ ከአብ ተካክሎ ልናየው ይገባል እንጂ ዝቅ
ልናደርገው አይገባም። «እነሆ ሰማይ ተከፍቶ፥ የሰው ልጅም
በእግዚአብሔር ቀኝ ቆሞ አያለሁ፤» ይላል። ጸሎታችንም፦
ጌታዬ ኢየሱስ ሆይ፥ ነፍሴን ተቀበል፤ . . . አቤቱ ይህን ኃጢአት
አትቊጠርባቸው፤» የሚል መሆን አለበት። የእግዚአብሔር
ቸርነት፥ የድንግል ማርያም አማለጅነት አይለየን። አሜን።